የአሜሪካ እና ኢራን ግጭት ዳግም ማገርሸቱን ተከትሎ የነዳጅ ዋጋ ጨመረ

የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images
አሜሪካ ከስድስት ሳምንታት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ እሁድ ምሽት ኢራን ላይ በፈጸመችው ጥቃት የመካከለኛው ምሥራቅ ግጭት ማገርሸቱን ተከትሎ በዓለም አቀፍ ገበያ የነዳጅ ዋጋ ጨመረ።
ባለፈው ሳምንት ቅናሽ ሲመዘገብበት የነበረው የነዳጅ ዋጋ ከአሜሪካ ጥቃት በኋላ የሁለት በመቶ ገደማ ጭማሪ ታይቶበታል።
የነዳጅ ዋጋ መለኪያ ተደርጎ የሚቆጠረው ብሬንት የአንድ በርሜል ድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ የ1.77 ዶላር ጭማሪ ታይቶበት በ89.87 ዶላር እየተሸጠ ነው።
አሜሪካ ከሐምሌ ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ በሚታወቅ ደረጃ በፈጸመችው የትናንቱ ጥቃት ላራክ በተባለው የኢራን ደሴት የሚገኙ ሁለት ማስወንጨፊያዎችን መምታቷን አስታውቃለች።
ይህንን ተከትሎም ኢራን በዮርዳኖስ እና በተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሠፈሮች ላይ ጥቃት መፈጸሟን ገልጻለች።
ስድስት ወራት ያስቆጠረው የኢራን ጦርነት በዓለም የነዳጅ ገበያ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ አሳድሯል። ከዓለም የነዳጅ እና ፈሳሽ የተፈጥሮ ጋዝ ምርት ውስጥ 20 በመቶ ገደማው የሚተላለፍበት ሆርሙዝ ወሽመጥ በኢራን በመዘጋቱ የአንድ በርሜል ነዳጅ ዋጋ ከ100 ዶላር በላይ ደርሶ ነበር።
ሁለቱ አገራት የሚፈጽሟቸው ጥቃቶች ረገብ ማለታቸውን ተከትሎ ደግሞ ቅናሽ ተስተውሏል።
ወሳኝ የባሕር መስመር የሆነው ሆርሙዝም በዛሬው ዕለት ጥቃት እንዳስተናገደ ተገልጿል። የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ባወጣው መግለጫ “በሆርሙዝ ወሽመጥ ደቡባዊ ክፍል በኩል ለማለፍ የሞከረ ሕገ ወጥ ነዳጅ ጫኝ መርከብ” ላይ ጥቃት መፈጸሙን አስታውቋል።
መርከቡ “በሁለት የተጠመዱ የባሕር ፈንጂዎች በመመታቱ በእሳት እንደተያያዘ እና ሙሉ በመሉ እንደቆመ” ገልጿል። በወሽመጡ ላይ የተጣለውን “የደኅንነት መመሪያ የሚጥሱ መርከቦች ዕጣ ከዚህ ያነሰ እንደማይሆንም” አስጠንቅቋል።
በአሜሪካ እና ኢራን መካከል ግጭት ማገርሸቱ እንዲሁም በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የሚታየው ሁኔታ፣ የባሕር መስመሩን ለማስከፈት ጥረት ሲያደርጉ የነበሩ አካላትን ስጋት ላይ ጥሏል።



