በኢራን ጦርነት 18 የአሜሪካ ወታደሮች መገደላቸው እና ከ600 በላይ መቁሰላቸው ተገለጸ
ፕሬዝዳንት ትራምፕ በኢራን ላይ ጥቃት እንዲፈጸም ካዘዙበት ያለፈው የካቲት ወዲህ 18 የአሜሪካ ወታደሮች መገደላቸውን እና ቢያንስ 624 ደግሞ መቁሰላቸውን ከአገሪቱ መከላከያ መስሪያ ቤት 'ፔንታገን' የወጣ መረጃ አመለከተ።
ጉዳቱ ከደረሰባቸው መካከል 417 በኢራን ላይ ከተካሄደው 'ኤፒክ ፊዩሪ’ ከተባለው ዘመቻ ጋር ሲያያዙ፣ 207 ያህሉ ደግሞ ‘በባሕር ማዶ ዘመቻዎች’ ላይ የተሳተፉ እንደሆነ ተጠቅሷል።
ባለፈው ሳምንት ፔንታገን በጦርነቱ ውስጥ የተገደሉ እና የቆሰሉ ወታደሮችን መረጃ የከለሰ ሲሆን፣ በዚህም በኢራን ጦርነት ከተገደሉ ወታደሮች መካከል የነበሩ አራት አባላቱን ስም በባሕር ማዶ ዘመቻ ላይ ከተገደሉት ዝርዝር ውስጥ አካትቷል።
የመከላከያ ሚኒስቴሩ የመረጃ ቋት ላይ በኢራን በተካሄደው ዘመቻ እስካለፈው ማክሰኞ ድረስ የተገደሉት 18 እና የቆሰሉ 482 ወታደሮች ዝርዝር ይዞ ቆይቷል። ከዚያ በኋላ ግን በተካሄደው ክለሳ ከሟቾቹ ዝርዝር ላይ አራት ወታደሮች ተቀንሰው ቁጥሩ 14 ሆኗል።
ምንም ዓይነት ማብራሪያ ሳይሰጥ በቆሰሉት እና በሞቱት ወታደሮች ስም ዝርዝር ላይ የተደረገው ለውጥ፣ 'ግልጽነትን የሚያደናቅፍ ነው' በሚል በቀድሞው የአገሪቱ ጦር ኃይል ከፍተኛ መኮንን ሌተናንት ቤን ሆጅስ ትችት ቀርቦበታል።
የፔንታገን ቃል አቀባይ ሾን ፓርኔል በበኩላቸው በጦር ጉዳተኞች አሃዝ ላይ የተደረገው ለውጥ “ጊዜያዊ የመረጃ መዛባት ነው” ብለዋል።
“የባሕር ማዶ ዘመቻዎች” የሚለው ዘርፍ ከዚህ ቀደም ያልነበረ ሲሆን በመከላከያ መስሪያ ቤቱ ድረ ገጽ ላይ የታየው ከእሁድ ጀምሮ መሆኑን አሶሺየትድ ፕሬስ ዘግቧል።
በዚህም ክፍል ላይ በቅርቡ ሕይወታቸውን ያጡ አራት ወታደሮችን ስም በሟች እንዲሁም 207 ደግሞ በቆሰሉ መዝግቧል። ነገር ግን የቆሰሉት ወታደሮች በኢራኑ ጦርነት የተጎዱ ስለመሆናቸው ግልጽ አይደለም።
አራቱ ወታደሮች የተገደሉት በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የተደረሰው ተኩስ አቁም ከፈረሰ በኋላ ነው። በድጋሚ በአሜሪካ ጥቃት የተፈጸመባት ኢራን በቀጣናው የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን ዒላማ አድርጋለች።
ኢራን ከአስር ቀናት በፊት ዮርዳኖስ ውስጥ የሚገኝ የአሜሪካ ጦር ሰፈር ላይ ባደረሰችው የሚሳዔል ጥቃት ሦስት ወታደሮች ተገድለዋል። አንዱ ደግሞ ኢራቅ ውስጥ የኢራን ድሮንን ለማክሸፍ በተወሰደ እርምጃ ወቅት ነበር የተገደለው።
አሜሪካ ለ13 ተከታታይ ቀናት በኢራን ላይ ጥቃት ስትፈጽም ኢራንም በምላሹ በቀጣናው ባሉ የአሜሪካ ወታደራዊ ተቋማት ላይ የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃት አድርሳለች።
ከአርብ ጀምሮ ባለፉት ሦስት ቀናት የአሜሪካ ጥቃት መቆሙን ተከትሎ ኢራንም የአጸፋ እርምጃዋን ጋብ አድርጋለች።