የኢራኑ ጠቅላይ መሪ በከፍተኛ ሁኔታ የተብላላ ዩራንየም ከአገራቸው እንዳይወጣ ወሰኑ

የፎቶው ባለመብት, Tasnim News Agency
ኢራን ጦርነቱን ለማስቆም የቀረበላትን በከፍተኛ ሁኔታ የተብላላ ዩራንየምን ወደ ውጭ ለመላክ የቀረበውን ሐሳብ ውድቅ ለማድረግ መወሰኗን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘገበ።
ሮይተርስ ሁለት ምንጮችን ጠቅሶ ባወጣው ዘገባ የኢራን ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻሜኒ በከፍተኛ ሁኔታ የተብላላ ዩራንየም ከአገር እንዳይወጣ ትዕዛዝ አስተላልፈዋል።
አሜሪካ ለሰላም ድርድር ካቀረበቻቸው ነጥቦች መካከል አንዱ ይሄው ጉዳይ ነው።
የጠቅላይ መሪው ውሳኔ የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕን አስተዳደር ሊያስቆጣ እና የድርድር ሒደቱን ሊያወሳስብ ይችላል።
ሮይተርስ ያነጋገራቸው የእስራኤል ባለሥልጣናት እንደሚሉት፤ ኢራን ያከማቸችው የተብላላ ዩራንየም ከአገሪቱ እንደሚወጣ ለእስራኤል ማረጋገጫ ሰጥተዋል።
የሰላም ስምምነት ላይ ኒውክሌር ጦር መሣሪያ የመሥራት ነጥብ ላይ የደረሰው የተብላላ ዩራንየም ከኢራን እንደሚወጣ መናገራቸው ተገልጿል።
ስለ ጉዳዩ የኢራን መገናኛ ብዙኃን እስካሁን ድረስ ዘገባ አላወጡም።
ኢራን ከአሜሪካ እና ከሌሎች ምዕራባውያን ጋር ለዘመናት ሲያወዛግብ የቆየው የኒውክሌር መርሃ ግብሯን ሙሉ ለሙሉ እንድታቆም እና ከጥቅም ውጪ እንድታደርግ የቀረበላትን ጥያቄ ባለመቀበሏ ነው።
በአሜሪካ እና በእስራኤል የተከፈተባትን ጦርነት ለማቆም ከቀረበላት ቅድመ ሁኔታ መካከልም እንዱ የኒውክሌር መርሃ ግብሯ ቢሆንም፤ ኢራን አልተቀበለችውም።




















