አሜሪካ ኩባን ‘ማስፈራራት’ እንድታቆም ቻይና አሳሰበች

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
አሜሪካ ኩባን “ማስፈራራት” እንዲሁም “ጫና ለማሳደር መሞከር” እንድታቆም ቻይና አሳሰበች።
የአሜሪካ ፍርድ ቤት የ94 ዓመቱ የቀድሞ የኩባ ፕሬዝዳንት ራውል ካስትሮ ላይ ክስ መመሥረቱን ተከትሎ ነው ቻይና ማሳሰቢያ የሰጠችው።
ከ30 ዓመት በፊት በኩባ እና በፍሎሪዳ መካከል ተመትተው ከወደቁ ሁለት አውሮፕላኖች ጋር በተያያዘ የቀድሞው የኩባ መሪ ላይ የተመሠረተው ክስ የአሜሪካ ዜጎችን ለመግደል ማሴር እና ሌሎችንም የያዘ ነው።
አራት ሰዎች የሞቱበት ክስተት የሁለቱን አገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት አሻክሯል።
የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኩባን ኮሚኒስት መንግሥት መገርሰስ እንደሚፈልጉ ተናግረዋል።
የቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጋዎ ጂያኩን “አሜሪካ በየአጋጣሚው ኩባን ማስፈራራት ማቆም አለባት” ብለዋል።
ቻይና “በጽኑ ኩባን ትደግፋለች። በውጭ ኃይሎች በማንኛውም አውድ ኩባ ላይ የሚደርስ ጫናን ቤይጂንግ ትቃወማለች” ሲሉም ተናግረዋል።
ቃል አቀባዩ “አሜሪካ ማዕቀብ እና የሕግ መዋቅርን በመጠቀም ኩባን ማስፈራራት እና ጫና ማሳደር ማቆም አለባት” በማለትም አክለዋል።
የኩባን ሉዓላዊነት እና ክብር ቻይና እንደምትደግፍ እንዲሁም የውጭ ኃይሎችን ጣልቃ ገብነት እንደምትቃወም ገልጸዋል።




















