በሰደድ እሳት ምክንያት ከ220 ሺህ በላይ ሰዎች ፈረንሳይ እና ስፔንን ለቅቀው እንዲወጡ ተደረገ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
በፈረንሳይ እና ስፔን በተነሳው ሰደድ እሳት ምክንያት ከ220,000 በላይ ሰዎች አካባቢያቸውን ለቅቀው እንዲወጡ መደረጉ ተገለጸ።
ከፈረንሳይ፣ ቦርዴውክስ አካባቢ ወደ 60,000 ገደማ ሰዎች ለቅቀው ወጥተዋል።
ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን የአገሪቱን መከላከያ ሠራዊት ያሰማሩ ሲሆን፤ በደቡብ ምሥራቅ ከሚገኙት ጊርዎንዴ እና ላንደርስ አካባቢዎች ወደ 200,000 ሰዎች ለቅቀው እንዲወጡ ተደርጓል።
በስፔን ማድሪድ አቅራቢያ የተነሳው ሰደድ እሳት የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች “መቆጣጠር ከሚችሉት በላይ” መሆኑ ተገልጿል።
ከመዲናዋ በስተምዕራብ ሦስት ሰደድ እሳቶች ተነስተዋል።
የስፔን መንግሥት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ደንግጎ 25,000 ሰዎች አካባቢውን ለቅቀው እንዲወጡ ሲደረግ፤ 40,000 ሰዎች ደግሞ ከቤት እንዳይወጡ ታዝዘዋል።
የማድሪድ ቀጣና ፕሬዝዳንት ኢዛቤል ዲዬዝ አዩሶ “በአካባቢያችን ከተከሰቱ ሰደድ እሳቶች የከፋው ነው” ብለዋል።
ከፍተኛ ሙቀት እና ንፋስ ተደራርበው እሳቱን እያስፋፉት እንደሚገኙ ገልጸዋል።
ሰደድ እሳቱ ወደ ሮቤልዶ ደ ቼቫላ እና ፈርሲንዳሌዝ ደ ላ ኦሊቪያ ግዛቶች እየተስፋፋ እንደሆነ ተገልጿል። እነዚህ አካባቢዎች ከመዲናዋ 50 ኪሎሜትር ይርቃሉ።
የፈረንሳይ የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች እንደገለጹት ሰደድ እሳቶቹ 19 ሺህ ሄክታር ደን አውድመው፣ 80 መኖሪያ ቤቶችን አጋይተዋል።

የፎቶው ባለመብት, EPA

የፎቶው ባለመብት, Reuters

የፎቶው ባለመብት, Getty Images



















