ዮሚፍ ቀጀልቻ የዓለም የወንዶች ግማሽ ማራቶን ክብረ ወሰንን በ29 ሰከንዶች አሻሻለ

ኢትዮጵያዊው ዮሚፍ ቀጀልቻ ዛሬ እሁድ በአርጀንቲና ዋና ከተማ ቦነስ አይረስ ውስጥ በተካሄደው የዓለም አትሌቲክስ የጎዳና ላይ ውድድር የዓለም የወንዶች የግማሽ ማራቶን ክብረ ወሰንን ሰበረ። ዮሚፍ አሁን ያሻሻለውን የግማሽ ማራቶን ክብረ ወሰንን ከሁለት ዓመት በፊት ስፔን ቫሌንሺያ ላይ በተደረገ ውድድር 57 ደቂቃ ከ30 ሰከንድ በሆነ ጊዜ በማሸነፍ ክብረ ወሰኑን ይዞት ነበር።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ዮሚፍ ቀጀልቻ የዓለም የወንዶች ግማሽ ማራቶን ክብረ ወሰንን በ29 ሰከንዶች አሻሻለ

    ዮሚፍ ቀጀልቻ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ዮሚፍ ቀጀልቻ

    ኢትዮጵያዊው ዮሚፍ ቀጀልቻ ዛሬ እሁድ በአርጀንቲና ዋና ከተማ ቦነስ አይረስ ውስጥ በተካሄደው የዓለም አትሌቲክስ የጎዳና ላይ ውድድር የዓለም የወንዶች የግማሽ ማራቶን ክብረ ወሰንን ሰበረ።

    ዮሚፍ አሁን ያሻሻለውን የግማሽ ማራቶን ክብረ ወሰንን ከሁለት ዓመት በፊት ስፔን ቫሌንሺያ ላይ በተደረገ ውድድር 57 ደቂቃ ከ30 ሰከንድ በሆነ ጊዜ በማሸነፍ ክብረ ወሰኑን ይዞት ነበር።

    ነገር ግን ከወራት በኋላ ኡጋንዳዊው ጄኮብ ኪፕሊሞ ክብረ ወሰኑን በማሻሻል ይዞት የቆየ ሲሆን፣ በተጨማሪም በዚህ ዓመት ፖርቹጋል ሊዝበን ውስጥ በተደረገ ውድድር ሰዓቱን በ10 ሰከንዶች በማሻሻል ወደ 57 ደቂቃ ከ20 ሰከንድ በማውረድ የክብረ ወሰኑን ባለቤትነቱ አጠናክሮት ነበር።

    የ29 ዓመቱ ኢትዮጵያዊ አትሌት ዮሚፍ ቀጀልቻ አሁን በተደረገው ውድድር ክብረ ወሰኑን በ29 ሰከንድ በማሻሻል 56 ደቂቃ ከ51 ሰከንድ ገብቷል።

    ይህ ዮሚፍ አርጀንቲና ላይ ያስመዘገበው አዲስ ክብረ ወሰን በዓለም አቀፉ አትሌቲክስ ስፖርት የበላይ አካል ተቀባይነትን አግኝቶ መጽደቅ ይኖርበታል።

    በ10 ሺህ ሜትር ውድድር የትራክ ውድድር የብር ሜዳሊያ ባለቤት የሆነው ዮሚፍ የ10 ሺህ ሜትር የወንዶች የጎዳና ላይ ውድድር ክብረ ወሰን ባለቤት ነው።

    በተጨማሪም በዚህ ዓመት ኬንያዊው ሴባስቲያን ሳዌ ለንደን ላይ ማራቶንን ከሁለት ሰዓት በታች በመግባት ታሪክ ባስመዘገበበት ውድድር ዮሚፍ ሁለተኛ በመውጣት ማራቶንን ከሁለት ሰዓት በታች የሮጠ ሁለተኛው ሰው ለመሆን ችሏል።

  2. ፕሬዝዳንት ፔዜሽኪያን ኢራን 'ሙሉ ጦርነት' ውስጥ ትገኛለች አሉ

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን

    የፎቶው ባለመብት, IRNA

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን እሁድ ዕለት ቴህራን “ሙሉ ጦርነት ውስጥ ትገኛለች” በማለት መንግሥት ችግሮችን ለመቅረፍ እየሞከረ መሆኑን ተናገሩ።

    ፔዜሽኪያን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን የሆነው ኢርና ባስተላለፈው ንግግራቸው ላይ “ሙሉ የምጣኔ ሃብት፣ የወታደራዊ እና የደኅንነት ጦርነት ውስጥ እንገኛለን” ብለዋል።

    መንግሥት በኢኮኖሚው ውስጥ ባሉ ችግሮች "እንደሚያፍር" ጨምረው ተናግረዋል።

    “ትራምፕ በኢራን ላይ እጅግ ከባድ ወይም እጅግ አስከፊ ማዕቀቦችን እንደሚጥሉ በቀላሉ ይናገራሉ” ያሉት ፔዜሽኪያን ቴህራን “የአቻ ባልሆነ ጦርነት” ውስጥ “ጸንታ በመቆም” የኢራንን ሕዝብ ለማገልገል እየጣረች መሆኑን አክለዋል።

    "ጠላት ኢራን ከወደቀች እንደ ቬንዙዌላ እንደምትሆን ገምግሞ ነበር። ይህ አለመከሰቱ ብቻ ሳይሆን በተጋዳይነቷ፣ በአንድነቷ እና በመተባበሯ ዓለምን ያስደነቀች ኃያል ሆናለች።" ሲሉ ፕሬዝዳንቱ ተናግረዋል።

    ቴህራን "ክፍፍልን፣ ግጭትንና ራስ ወዳድነትን ለማስወገድ በሙሉ ኃይሏ እየሰራች ነው" ብለዋል።

    ኢራን እና አሜሪካ በሰኔ ወር በፓኪስታን እና በኳታር አሸማጋይነት የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል።

    ስምምነቱ በየካቲት ወር የተጀመረውን ጦርነት አስወግዶ የመጨረሻውን ስምምነት ለማሳካት ያለመ ነበር።

    ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ለዓለም አቀፍ የነዳጅ እና የጋዝ ምርት ወሳኝ መተላለፊያ የሆነው የሆርሙዝ ወሽመጥን ለማስከፈት በቀረቡ ሃሳቦች እና አተገባበሩ ላይ በተፈጠሩ አለመግባባቶች የተነሳ ውይይቱ ተቋርጧል።

  3. የፓኪስታን ጦር አዛዥ ነገ ሰኞ ወደ ኢራን ሊያቀኑ ነው

    የፓኪስታን ጦር አዛዥ አሲም ሙኒር

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, የፓኪስታን ጦር አዛዥ አሲም ሙኒር

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ እስማኤል ባጋይ የፓኪስታን ጦር አዛዥ አሲም ሙኒር የቀጣናውን ሰላምና ደኅንነት ለማስቀጠል የሚደረገውን ጥረት ለማገዝ ሰኞ ቴህራን እንደሚገቡ አስታወቁ።

    አሜሪካ እና እስራኤል የካቲት 21፣ 2018 ዓ.ም. በኢራን ላይ የጀመሩትን ጦርነት ለማስቆም በሚደረገው ድርድር ውስጥ ፓኪስታን የአሸማጋይነት ሚና እየተጫወተች ትገኛለች።

    ሁለት የፓኪስታን መንግሥት ምንጮችም የጦር አዛዡ ወደ ቴህራን እንደሚያቀኑ ለሮይተርስ አረጋግጠዋል።

    የመጀመርያው ምንጭ ኢራን እና ፓኪስታን በቀጥታ ንግግር እያደረጉ መሆኑን አስታውቀዋል።

    ሁለተኛው ምንጭ በበኩላቸው ንግግሩ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ጠንከር ያለ ማዕቀብ እንደሚጥሉ የተናገሩትን ጨምሮ ሌሎች በቅርቡ የተከሰቱ ጉዳዮች ላይ እንደሚያተኩር ገልጸዋል።

    ምንጩ አክለውም “እርሳቸው (ሙኒር) ከኢራን መሪዎች ጋር ስለሰላም፣ በኢስላማባድ የመግባቢያ ስምምነት፣ በትራምፕ ማስጠንቀቂያ እንዲሁም በፓኪስታን-ቱርክ-ሳዑዲ አረቢያ ስምምነት እና በሁቲዎች ጉዳይ ዙሪያ ይወያያሉ።” ብለዋል።

    የጦር አዛዡ ጉብኝት የሚደረገው አሜሪካ ማዕቀብ ለመጣል ማቀዷን ካስታወቀች በኋላ እና ኢራንም ለዚህ እርምጃ ወታደራዊ ምላሽ እንደምትሰጥ በመዛቷ በከፍተኛ ሁኔታ ውጥረት ባየለበት ወቅት ነው።

    አሜሪካ ሰኞ ዕለት የምትጥለውን ማዕቀብ ዝርዝር ይፋ ለማድረግ ማቀዷን ያስታወቀች ሲሆን የዋሺንግተን ባለሥልጣናት ኢራን ላይ ከተጣሉት ሁሉ “የከፋው” ሊሆን ይችላል ብለዋል።

    ትራምፕ ለኢራን የትኛውንም “ድጋፍ” የሚያደርግ ማንኛውም አገር፣ ምጣኔ ሃብታዊ መዘዝ እንደሚጠብቀው ያስጠነቀቁ ሲሆን ቴህራንን ከቀሪው ዓለም ለመነጠል ማሰባቸውን ይፋ አድርገዋል።

    በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚያልፉ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ የቀነሰ ሲሆን የኢራን ምጣኔ ሃብትም ከዚህ ቀደም በተጣሉባት ማዕቀቦች የተነሳ ክፉኛ ተጎድቷል።

  4. የ7 ዓመት ልጁን በጃፓኑ ትልቅ ተራራ 2 ሺህ ሜትር ከፍታ ላይ አስቀምጦ ጉዞውን የቀጠለ አባት መነጋገሪያ ሆነ

    ፉጂ ተራራ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ታዳጊው በጃፓን ትልቅ ተራራ ላይ የተገኘው ብቻውን ነበር

    የሰባት ዓመት ልጁን ለስላሳ እና ብስኩት ሰጥቶ በጃፓን ትልቅ ተራራ ላይ ብቻውን ትቶ የሄደ አባት ከፖሊስ ማስጠንቀቂያ ተሰጠው።

    የ48 ዓመቱ አባት ከልጆቹ ጋር ተራራ እየወጡ ሳለ ታዳጊ ልጁ እንደደከመው ከገለፀለት በኋላ እዚያው ባለበት እንዲቆይ የሚበላው እና የሚጠጣው አስይዞ ከትልቁ ልጁ ጋር ጉዞውን መቀጠሉ ተዘግቧል።

    የ7 ዓመቱ ሕፃን በፉጂ ተራራ ላይ ጭጋጋማ እና ዝናባማ በሆነ ሁኔታ ውስጥ በ2 ሺህ ሜትር ከፍታ ባለው ቦታ ላይ ለብዙ ሰዓታት ተቀምጦ ታይቷል።

    በተራራው ላይ ያሉ ሠተራኞች ካገኙት በኋላም ለፖሊስ አሳውቀዋል።

    አባቱ ተራራው ላይ ደርሶ ከልጁ ጋር ሲገናኝ ፖሊሶች ወቅሰውታል። ታዳጊውም ለስምንት ሰዓታት "ደክሞ እና ተጨንቆ" እንደነበር ተናግሯል። አባት በችኮላ ለወሰነው ውሳኔ ይቅርታ ጠይቋል።

    ፉጂ ተራራ ከባሕር ጠለል በላይ በ3 ሺህ 776 ሜትር ከፍታ ላይ የሚገኝ ሲሆን በቅርብ ዓመታት ውስጥ በርካታ አደጋዎች ተከስተውበታል።

    ሐምሌ ወር ላይ አንዲት የ99 ዓመት አዛውንት ወድቀው ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባቸዋል።

    ባለፈው ዓመትም የ27 ዓመት የዩኒቨርሲቲ ተማሪ የጠፋበትን ሞባይል ለመፈለግ በመመላለስ በአራት ቀናት ውስጥ ሁለት ጊዜ ከሞት ተርፏል።

    ፉጂ ተራራ ከቶኪዮ በስተደቡብ ምዕራብ የሚገኝ ንቁ እሳተ ገሞራ ያለበት አካባቢ ሲሆን እአአ በ2013 በዓለም ቅርስነት ተመዝግቧል።

    ከቴት ተራራ እና ከሃኩ ተራራ ጋር በመሆን “የሦስቱ ባህላዊ ቅዱስ ተራሮች” አካል ነው።

    በየዓመቱ ወደ 200 ሺህ ገደማ የሚጠጉ ሰዎች ወደ ተራራው ይወጣሉ።

  5. ቦትስዋና የሩሲያን ጦር ለመቀላቀል በሚሞክሩ ዜጎቿ የተነሳ ስጋት እንዳደረባት አስታወቀች

    የቦትስዋና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ሚኒስትር ፌንዮ ቡታሌ

    የፎቶው ባለመብት, Anadolu via Getty

    የምስሉ መግለጫ, የቦትስዋና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ሚኒስትር ፌንዮ ቡታሌ

    ቦትሰዋና የሩሲያን ጦር ለመቀላቀል የሚሄዱ ስምንት ዜጎቿን ማስቆሟን የአገሪቱ ዓለም አቀፍ ግንኙነት ሚኒስትር ፌንዮ ቡታሌ ተናገሩ።

    ሚኒስትሩ አርብ ዕለት ለደቡብ አፍሪካ አገራት ፓርላማ "በሩሲያ እና በዩክሬን ግጭት ላይ እንዲሳተፉ የሚመለመሉ ወይም ለምልመላ ዒላማ የሚደረጉ የቦትስዋና ዜጎች ቁጥር መጨመሩ መንግሥትን ከፍተኛ ስጋት ውስጥ ጥሎታል።" ብለዋል።

    "ዜጎቻችን በቅጥር፣ በሥልጠና ወይም በደኅንነት ሥራ ሽፋን በሚቀርቡ ማባበያዎች ተታለው፣ በጭራሽ አስበውት በማያውቁት የውጊያ ግንባር እንዲሰለፉ ስለመደረጋቸው የሚያሳስቡ ሪፖርቶች እየደረሱን ነው።" ሲሉ አክለዋል።

    ቡታሌ "እስካሁን ድረስ ወደ 22 የሚጠጉ የቦትስዋና ዜጎች በእነዚህ አማላይ የቅጥር ማባበያዎች ተታልለው ሄደዋል" ብለዋል።

    "ከወዳጅ አገራት ጋር በመሆን ባደረግነው ጥብቅ ክትትልና የቅርብ ትብብር፣ በሰር ሴሬትሴ ካማ፣ በኦአር ታምቦ እና በአዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያዎች ጉዟቸውን ለመጀመር በተቃረቡበት ወቅት፣ ወደ ጦርነት ውስጥ ከመግባታቸው ጥቂት ቀደም ብለን፣ ስምንት ግለሰቦችን ማስቆምና መመለስ ችለናል።" ሲሉ አክለው ገልጸዋል።

    ከቅርብ ዓመታት ወዲህ አታላይ በሆኑ የሰዎች ዝውውር መስመሮች አማካኝነት በሺዎች የሚቆጠሩ አፍሪካውያን ወደ ሩሲያ ጦር ሠራዊት እንዲቀላቀሉ መደረጉ ከፍተኛ ቁጣንና ዲፕሎማሲያዊ ውጥረትን አስከትሏል።

  6. የኢራን ፕሬዚዳንት ቴህራን ከአቋሟ ሸብረክ አትልም በማለት “ጦርነትም ሰላምም የሌለበት ሁኔታ” እንዲያበቃ ጥሪ አቀረቡ

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን

    የፎቶው ባለመብት, IRNA

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን ቅዳሜ ዕለት ቴህራን ምንም ዓይነት ስምምነት የማድረግ ፍላጎት እንደሌላት ገልጸው "ጦርነትም ሆነ ሰላም ከሌለበት" ሁኔታ መውጣት እንደሚያስፈልግ መናገራቸውን የአገሪቱ የዜና ተቋም ኢርና ዘግቧል።

    ፔዜሽኪያን የኢራን ባለሥልጣናት ከዚህ ሁኔታ እንዴት መውጣት እንደሚቻል እና የኢራንን መርሆዎችና እሴቶች በሚጠብቅ፣ እንዲሁም ተቃዋሚ ወገኖች ሌላ ጥቃት ለመፈጸም እንዳያስቡ በሚያደርግ መልኩ እንዴት ስምምነት ላይ መድረስ እንደሚቻል በየቀኑ ማለት በሚቻል መልኩ ሲወያዩ ቆይተዋል ብለዋል።

    ጦርነት ምንም ዓይነት መፍትሄ እንደማያመጣ የገለጹት ፕሬዚዳንቱ፣ በተመሳሳይም ውጊያው ዳግም ሊያገረሽ ይችላል የሚለው ላይ ለረዥም ጊዜ እርግጠኛ ሳይሆኑ መቆየት በአገሪቱ ኢኮኖሚ ላይ ጫና እያሳደረ መሆኑን ተናግረዋል።

    ፔዜሽኪያን፣ ግጭት ሊያገረሽ ይችላል የሚል ስጋት እስካለ ድረስ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ አስቸጋሪ እንደሚሆን አስጠንቅቀው፤ የአገሪቱን ጥንካሬ በመጠበቅ ሁኔታውን በምክንያታዊነት መፍታት እንደሚያስፈልግ አጽንኦት ሰጥተዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ከዩናይትድ ስቴትስ ጋር በቅርቡ የተደረገውን የመግባቢያ ሰነድ በመደገፍ፣ ሰነዱ እጅ መስጠትን የሚያመላክት ወይም ቴህራን ስምምነት ላይ እንድትደርስ የሚያስገድድ አንቀጽ እንደሌለው ገልጸዋል።

    ኢራን እና አሜሪካ በሰኔ ወር በፓኪስታን እና ኳታር አደራዳሪነት በየካቲት ወር የተጀመረውን ጦርነት የሚያስቆም እና ወደ መጨረሻው ስምምነት ላይ ለመድረስ ወደሚያስችል ድርድር ይመራል የተባለ የመግባቢያ ሰነድ ተፈራርመው ነበር።

    የመግባቢያ ስምምነቱ አተገባበር ላይ መግባባት ባለመደረሱ እንዲሁም በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል መርከቦች እንዲያልፉ ማድረግ ባለመቻሉ ንግግሮች ሳይካሄዱ ቀርተዋል።

  7. አሜሪካ አዳዲስ ማዕቀቦችን ለመጣል ማቀዷን ኢራን አወገዘች

    የአሜሪካ ጦር አውሮፕላኖች

    የፎቶው ባለመብት, CENTICOM

    ኢራን ቅዳሜ ዕለት ኢኮኖሚዋ ላይ ተጨማሪ ጫና ሊፈጥሩ እና ቻይናን ጨምሮ በዋና ዋና የንግድ አጋሮቿ ላይ ተጽዕኖ ሊያሳድሩ የሚችሉ አዳዲስ ማዕቀቦችን አሜሪካ ለመጣል ማቀዷን አወገዘች።

    ከተጀመረ ስድስት ወር የሞላው የኢራን ጦርነት አሁን የመሳሪያ ተኩስ መሰማት ቢያቆምም ሁለቱም ተፋላሚ ወገኖች ወደ ስምምነቱ ጠረጴዛ ለመምጣት በጣም ሩቅ ይመስላሉ።

    ቴህራን ፈቃድ ያላገኙ ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን እንደምታጠቃ በመዛቷ በሆርሙዝ በኩል የሚያልፍ ነዳጅ እንደቆመ ሲሆን የአገሪቱም ምጣኔ ሃብት በተደጋጋሚ ማዕቀቦች የተነሳ ከፍተኛ ጫና ውስጥ ነው።

    የአሜሪካው ገንዘብ ሚኒስትር ስኮት ቤስንት በኢራን ላይ “በታሪክ ታይቶ የማይታወቅ ጠንካራ ማዕቀብ” ለመጣል ከዛቱ በኋላ ሰኞ ዕለት ጋዜጣዊ መግለጫ እንደሚሰጡ ይጠበቃል።

    ኢራን ከምትልከው ነዳጅ ከ80 በመቶ በላይ የምትገዛው ቻይና ከዋሽንግተን ጋር እንድትተባበር ቤሰንት አሳስበዋል። ቤጂንግ በበኩሏ አሜሪካ ዲፕሎማሲያዊ አካሄድን እንድትከተል ጥሪ አቅርባለች።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ እስማኤል ባጋይ ቅዳሜ ዕለት እንደተናገሩት፣ አሜሪካ በቅርቡ ልትጥላቸው ያሰበቻቸው አዳዲስ የኢኮኖሚ ማዕቀቦች "በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ውስጥ ባሉ ሁሉም ሉዓላዊ አባል አገራት ላይ የድንበር ተሻጋሪ የበላይነትን የመጫን ሙከራ" ናቸው ብለዋል።

    "እንደዚህ ዓይነት በሦስተኛ አገር ላይ የሚጣሉ ማዕቀቦች በዓለም አቀፍ ሕግ ውስጥ ምንም ዓይነት መሠረት የላቸውም" ሲሉ በኤክስ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሑፍ ገልጸዋል።

    የኢራን ከፍተኛ ብሔራዊ ደኅንነት ምክር ቤት ጸሐፊ ​​ሞህሰን ረዛኢ በበኩላቸው ቴህራን አሜሪካን በሚረዱ አገራት ላይ ጥቃት እንደምትሰነዝር ለአገሪቱ ቴሌቪዥን ተናግረዋል።

    ሬዛኢ "በአቅራቢያችን የሚገኙ አገራት ሁሉ የአሜሪካን የኢኮኖሚ ጦርነት ጋር እንዳይቀላቀሉ እያሳሰብን ነው፤ አለበለዚያ እንደ ጠላት እንቆጥራቸዋለን" ብለዋል።

    ለኢራን "ማንኛውንም ዓይነት ድጋፍ” ለሚሰጥ አገር ኢኮኖሚያዊ መዘዞች እንደሚያጋጥሙት ያስጠነቀቁት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፣ ዋሽንግተን በግጭቱ ውስጥ "ምን እንደሚከሰት" እየተከታተለች መሆኗን አርብ ዕለት ተናግረዋል።

    ትራምፕ ስለ ኢራን ሲናገሩ “ከስምምነት ላይ መድረስ በብርቱ ይፈልጋሉ፤ ነገር ግን በእኔ እምነት ትክክለኛውን ስምምነት ለመፈረም ዝግጁ አይደሉም” ብለዋል።"

  8. “ኢትዮጵያ ከዚህ በኋላ መንገዷ መስቀለኛ ሳይሆን ቀጥ ያለ ነው”- ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ

    ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ በምክክሩ ለዘመናዊት ኢትዮጵያ “ይበጃል” የተባሉ ምክረ ሀሳቦች እንደቀረቡ እና ይህም “ዘመን ተሻጋሪ አዲስ ሐሳብ የሚወለድበት” መንገድ እንደሆነ ተናግረዋል።

    “ኢትዮጵያውያን የምናደርገው ውይይት ወደ እርጋታ እና ስክነት” የሚወስድ ነው ያሉት ፕሬዝዳንቱ በሒደቱ “የቱማታ ስሜት የለም፣ ያዙኝ ልቀቁኝ ስሜት የለም” ብለዋል።

    የኢትዮጵያ የፖለቲካ አውድ “ከተቃርኖ፣ ከደመኛነት ወደ ይቅርታ” እንዲራመድ መሠረት የጣለ ምክክር ነው ሲሉም ተደምጠዋል።

    “የተለምዶው የፖለቲካ ማጠንጠኛ የአምባጎሮ፣ የአመጽ፣ የነፍጥ አዙሪት ወደ ሰላም እና መደማመጥ [እንዲሻገር] በር ከፍቷል” ብለዋል።

    ‘ኢትዮጵያ ልትፈርስ ነው’ ኢትዮጵያ ልትበተን ነው’ የሚለው ለዘመናት ሲሰማ የቆየ ንግግር እንዳለ ጠቅሰው ይህ ግን ንግግሩን የሚያሰሙን አካላት “የእንጀራቸው መንገድ እንጂ የኢትዮጵያ መንገድ አይደለም” ብለዋል።

    ኢትዮጵያ ከዚህ በኋላ መንገዷ “መስቀለኛ ሳይሆን ቀጥ ያለ ነው” ሲሉም ተናግረዋል።

  9. “ንግግር ጦርነትን ይቀድማል”- ኦሊሴጉን ኦባሳንጆ

    የትግራይን ጦርነት ለመግታት በተካሄደው ድርድር ጉልህ ሚና የተጫወቱት የቀድሞ የናይጄሪያ ፕሬዝዳንት እና የአፍሪካ ኅብረት ከፍተኛ ተወካይ ኦሊሴጉን ኦባሳንጆ “የቀደመውን ጦርነት፣ ግጭት፣ ነውጥ፣ ደኅንነት ማጣት፣ ክፍፍል፣ ውደመት፣ መድልዎ ወደኋላ እንተወው፤ ይበቃናል” ሲሉ ተናግረዋል።

    ኦባሳንጆ ብሔራዊ አንድነት፣ ደኅነንት፣ አካታችነት፣ የሰዎች ደኅንነት እና ክብር መስፈን እንዳለበት ገልጸውም “ንግግር ጦርነትን፣ ግጭትን፣ ነውጥን ይቀድማል” ብለዋል።

  10. “ክርክሩ ሲያልቅ አንድ አገር ነው የሚቀራችሁ”- ኡሁሩ ኬንያታ

    የቀድሞው የኬንያ ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ

    የቀድሞው የኬንያ ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ የኢትዮጵያ የምክክር ሒደት የጎረቤት አገራትን የሚያነሳሳ መሆኑን ተናግረዋል።

    ዛሬ ቅዳሜ እየተካሄደ ባለው የአገራዊ ምክክር የመዝጊያ ስነ ስርዓት ላይ ተገኝነተው ንግግር ያደረጉት ኡሁሩ፣ “አዲስ አበባ ስትታረቅ. . . ጎረቤት አገራት ለራሳቸው ትግል ማቆሚያ ይጠቀሙበታል” ብለዋል።

    “ኢትዮጵያ ሁሉም ሕዝቦቿ ያስፈልጓታል” ያሉት ኬንያታ፤ የፖለቲካ ልዩነት ግጭት የሚያደርሰውን ጉዳት “እንደማይመጥን” በንግግራቸው ጠቅሰዋል።

    ከዚህ ቀደም በነበረው ግጭት ለውይይት በሩን በመክፈት አፍሪካውያን የነበራቸውን ሚና ጠቅሰው “ክርክሩ ሲያልቅ አንደ አገር ነው የሚቀራችሁ” ብለዋል።

    ለአፍሪካውያን ችግር "ከውጭ በሻንጣ የሚመጣ መፍትሔ" ሳይሆን አህጉራዊ መፍትሔ እንደሚበጅ ተናግረዋል።

    የኢትዮጵያ ጉዞ "አፍሪካን የሚያነሳሳ ይሁን" ሲሉም አክለዋል።

  11. “ታሪካዊ ስብራትን በጠመንጃ ሳይሆን በምክከር ለመፍታት አዲስ ምዕራፍ ከፍተናል”- ሒሩት ገብረሥላሴ

    የኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ኮሚሽን ምክትል ዋና ኮሚሽነር ሒሩት ገብረሥላሴ፤ የምክክር ሒደቱ “በአገሪቱ ፖለቲካ እና ማኅበራዊ ታሪክ አዲስ ምዕራፍ የከፈተ ነው” ብለዋል።

    “ታሪካዊ ስብራት እና የሐሳብ ልዩነት በጠመንጃ እና በኃይል ሳይሆን በምክከር ለመፍታት አዲስ ምዕራፍ ከፍተኛል” ሲሉም ተናግረዋል።

    “ለዘመናት የገጠሙ አለመግባባቶች በኃይል እና በመገፋፋት ሳይሆን በምክክር እና በመደማመጥ መፈታት እንደሚችሉ በተግባር ያረጋገጡበት አዲስ የፖለቲካ ባህል ነው” በማለትም የምክክር ሒደቱ ለወደፊት የሚኖረውን ሚና ገልጸዋል።

    ምክትል ኮሚሽነሯ ሒሩት እንደተናገሩት በምክክሩ “ማንኛውም የኅብረተሰብ ክፍል ሳይገለል የሁሉም ድምጽ እንዲከበር” ተሠርቷል።

    ጉባዔው “የመላው ኢትዮጵያ እውነተኛ መድረክ” እንዲሆን መደረጉንም ጠቅሰዋል።

    በውይይቱ ወቅት የተነሱ ምክረ ሐሳቦችን ለነገዋ ኢትዮጵያ “መሠረት የሚጥሉ” ሲሉ ገልጸዋቸዋል።

    ምክክሩ ቀላል እንዳልነበረ የተናገሩት ሒሩት የዕይታ ልዩነቶች ቢኖሩም “ስኬታችን በአንድ ሐሳብ መስማማት ሳይሆን በሐሳብ ልዩነት እርስ በርስ በመደማጥ የጋራ መፍትሔ መፈለግ ነው” ብለዋል።

    የቀረቡት ምክረ ሀሳቦች በመንግሥት እና በሚመለከታቸው አካላት “ተግባራዊ ይደረጋሉ” ብለው እንደሚያምኑም ተናግረዋል።

    ምክትል ኮሚሽነሯ “የምንለያይበት ጉዳይ ቢኖርም የምንጋራት አገር አንድ ናት” ብለዋል።

    “የጀመርነውን የመደማመጥ መንገድ ማስቀጠል ያስፈልጋል” ሲሉም ተናግረዋል።

  12. “በመሣሪያ ያሸነፈ ኃይል የለም፤ ማሸነፍ የሚቻለው በንግግር ነው”- ፕ/ር መስፍን አርአያ

    የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ

    የፎቶው ባለመብት, ebc

    የሀገራዊ ምክክሩ የመዝጊያ ሥነ ሥርዓት ዛሬ ነሐሴ 16 ቀን 2018 ዓ. ም. ሲከናወን የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ “ከተመካከርን፣ ከተነጋገርን፣ ከተደማመጥን፣ ውጤት ላይ እንደምንደርስ ያየንበት ነው” ሲሉ ገልጸውታል።

    አራት ሺህ ሰዎች “ለዚህ ሁሉ ቀናት ይቆያሉ?” የሚል ጥያቄ ቢነሳም ምክክሩን ማጠናቀቅ መቻሉን ጠቅሰው፤ በምክክሩ የተነሱ አጀንዳዎች በየክልሉ እና በሁለቱ ከተሞች ለሚደረግ ምክክር መነሻ እንደሚሆኑ ገልጸዋል።

    የምክክር ሒደቱ “ይሄ የወንዝ ጥያቄ አይደለም. . . ይሄ የጋራ ጥያቄ ነው” በሚል ዐውድ እንደተከናወነ የተናገሩት ፕ/ር መስፍን “በመሣሪያ ያሸነፈ ኃይል የለም። ማሸነፍ የሚቻለው በንግግር ነው” ሲሉም ተናግረዋል።

  13. የኔቶ አባላት ሆርሙዝ ወሽመጥን በተመለከተ ያሉ አማራጮች ላይ መወያየታቸው ተዘገበ

    የሆርሙዝ ወሽመጥ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በሆርሙዝ ወሽመጥ በነጻነት መንቀሳቀስ የሚቻልበትን መንገድ ለማሳለጥ ያለመ እና በሰሜን አትላንቲክ ጦር ቃልኪዳን (ኔቶ) ከፍተኛ ኮማንደር የተመራ ውይይት መደረጉን ሮይተርስ ዘገበ።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል የከፍተኛ ኮማንደሩን ቃል አቀባይ ጠቅሶ እንደዘገበው፤ ያለፈው ረቡዕ በአውሮፓ አጋር አገራት ዋና መሥሪያ ቤት በከፍተኛ የመከላከያ አመራሮች ደረጃ ውይይት ተደርጓል።

    አጋር አገራቱ በሆርሙዝ ወሽመጥ በነጻነት ለመጓጓዝ እንዲቻል ምን አስተዋጽኦ ማድረግ እንደሚችሉ በውይይቱ መነሳቱ ተገልጿል።

    የአጋር አገራቱ ከፍተኛ ኮማንደር ቃል አቀባይ የሆኑት የአሜሪካ አየር ኃይል መሪ አሌክሱስ ግራንክዊች ትናንት አርብ “ይሄ የኔቶ ተልዕኮ እንዳልሆነ ግልጽ መሆን አለበት” ብለዋል።

    “ኔቶ አጋሮችን አንድ ላይ የማምጣት እና አቅማቸውን የመረዳት ልዩ ብቃቱን ተጠቅሞ ያመቻቸው ነው” ሲሉም አክለዋል።

    የኔቶ አገራት በኢራን ጦርነት በቀጥታ ላለመሳተፍ እየሞከሩ ሲሆን፤ የሆርሙዝ ወሽመጥ የሚከፈትበትን አማራጭ መንገድ መፈለግ ግን ቀጥለዋል።

    ግጭቱ ከረገበ በኋላ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ደኅንነቱ የተጠበቀ ጉዞን ለማረጋገጥ የአገራት ትብብር እንዲኖር ለማስቻል ፈረንሳይ እና ዩናይትድ ኪንግደም ጥረት አድርገዋል።

    ዘላቂ ስምምነት ላይ ለመድረስ ግን የግድ የኢራን ፈቃደኛነት ያስፈልጋል።

  14. ሩሲያ በዩክሬን ባደረሰችው ጥቃት ቢያንስ ሁለት ሰዎች መገደላቸው ተገለጸ

    በዩክሬን የደረሰው ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, Oleksandr Hanzha / Dnipropetrovsk regional administration

    ሩሲያ በዩክሬን ላይ ባደረሰችው ጥቃት ቢያንስ ሁለት ሰዎች እንደተገደሉ እና ዘጠኝ ሰዎች እስካሁን የደረሱበት እንዳልታወቀ ተገለጸ።

    ከአንድ ቀን በፊት በመገበያያ ማዕከል ላይ በተፈጸመ ጥቃት 16 ሰዎች ተገድለዋል።

    በኪቭ የባለስቲክ ሚሳዔል ማስጠንቀቂያ ከተሰጠ በኋላ በመጋዘን በተነሳ እሳት ሳቢያ አንድ ግለሰብ መገደሉ ተገልጿል። ሌላ ግለሰብ ደግሞ ዛፖሪዣህ ውስጥ በድሮን ጥቃት ተገድሏል ተብሏል።

    የሩሲያ መከላከያ ሚኒስቴር እንዳለው የመጓጓዣ መሠረት ልማት እና መጋዘኖች ላይ ያነጣጠረ መጠነ ሰፊ ጥቃት ተፈጽሟል።

    ከአንድ ቀን በፊት በክሪቪይ የሚገኝ እና በርካታ ሰዎች የሚንቀሳቀሱበት መገበያያ ማዕከል ላይ ተከታታይ የድሮን ድብደባ ደርሷል።

    ፕሬዝዳንት ቮሎድሚር ዜሌንስኪ “እጅግ የጨለመ እና አሳፋሪ” ሲሉ ጥቃቱን አውግዘዋል።

    በትውልድ ከተማቸው የተፈጸመው ጥቃት በሁለት ዙር እንደደረሰ እና ሁለተኛ ጥቃት የድንገተኛ ጊዜ ሠራተኞችን ዒላማ እንዳደረገ ተናግረዋል።

    ቢቢሲ ያረጋገጣቸው ተንቀሳቃሽ ምሥሎች እንደሚያሳዩት እየነደደ ያለ መገበያያ ማዕከል ላይ ሌላ ድሮን ተተኩሷል።

    በዲኒፕሮፔትሮቮስክ ከተማ በሚገኝ ግዙፍ መገበያያ ማዕከል በደረሰ ጥቃት 23 ሕጻናትን ጨምሮ 130 ተገድለዋል።

  15. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ሆርሙዝ “የአሜሪካ ግዛት ነው” አሉ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከኢራን ጋር በሚደረገው ጦርነት የፍጥጫ ማዕከል የሆነው የሆርሙዝ ወሽመጥ “የአሜሪካ ግዛት ነው” ሲሉ ተናገሩ።

    አርብ ዕለት በደቡብ ካሪላይና ግዛት በተካሄደ የምርጫ ቅስቀሳ ዘመቻ ላይ የተገኙት ፕሬዝዳንቱ “በአሁኑ ሰዓት የሆርሙዝ ወሽመጥን እንደ የአሜሪካ ግዛት ነው የምመለከተው። የአሜሪካ ግዛት ነው” ሲሉ ለተሰበሰበው ደጋፊ ተናግረዋል።

    ከዓለም ነዳጅ ምርት ውስጥ 20 በመቶ ገደማው የሚተላለፍበት የሆርሙዝ ወሽመጥ በኢራን እና ኦማን መካከል የሚገኝ ወሳኝ የባሕር መስመር ነው። የካቲት ላይ በአሜሪካ እና እስራኤል ጥቃት የተከፈተባት ኢራን ከወሰደቻቸው የአጸፋ እርምጃዎች አንዱ ይህንን ወሳኝ የባሕር በር መዝጋት ነው።

    በዚህም የተነሳ በዓለም የኤነርጂ ገበያ ላይ መስተጎጓል ተፈጥሯል። የነዳጅ ዋጋም ከፍተኛ ጭማሪ ታይቶበት ቆይቷል።

    ትራምፕ በትናንቱ ንግግራቸው “ከኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ጋር እንደጨረስን፣ የነዳጅ ዋጋ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከነበረበት ጭምር ዝቅተኛ ይሆናል” ብለዋል።

    በተጨማሪም ትራምፕ አገራቸው ኢራን የኒውክሌር መሣሪያ እንዳይኖራት ማድረጓን ገልጸዋል። “ኢራን የኒውክሌር መሣሪያ እንዲኖራት ልንፈቅድ አንችልም። [መሣሪያውን ከታጠቀች ግን] በጣም መጥፎ ነገር ታያላችሁ። ስለዚህ ሄደን አስቁመናቸዋል” ሲሉ ተደምጠዋል።

    የኒውክሌር መሣሪያ የመስራት ዕቅድ አላት በሚል የምትከሰሰው ኢራን የኒውክሌር ፕሮግራሟን የምትጠቀመው ለሰላማዊ ዓላማ እንደሆነ በተደጋጋሚ ገልጻለች።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ይህንን ንግግር ያደረጉት በሁለቱ አገራት መካከል የሚታየው ውጥረት ዳግም እያንሰራራ ባለበት ወቅት ነው። የፕሬዝዳንቱ አስተዳደር የኢራንን ኢኮኖሚ “የሚያደቅቅ” እና አገዛዙን “የሚያፈርስ” ኢኮኖሚያዊ ማዕቀብ እንደሚጥል አስታውቋል።

    ትራምፕ አርብ ዕለት ከጋዜጠኞች ጋር በነበራቸው ቆይታ፣ አሜሪካ ኢራን ላይ ኢኮኖሚያዊ ጫናን ወደመጨመር ብታዘነብልም ቴህራን ላይ የሚወሰድ ወታደራዊ ዘመቻ አሁንም አማራጭ መሆኑን ተናግረዋል።

    አክለውም ኢራን “ስምምነት ማድረግ በጣም ትፈልጋለች፤ ነገር ግን በእኔ እምነት ትክክለኛውን ስምምነት ለማድረግ አልተዘጋጁም” ብለዋል።

    “ገንዘብ የላቸውም፣ የባህር ኃይል የላቸውም፣ የአየር ኃይል የላቸውም። ለወታደሮቻቸው፣ ለፖሊስ አባላቶቸቻው ደመወዝ እየከፈሉ አይደለም። 350% የዋጋ ግሽበት አላቸው። ስለዚህ ምን እንደሚከሰት የምናየው ይሆናል” ሲሉ በፕሬዝዳንታዊ አውሮፕላናቸው ከመሳፈራቸው በፊት ተናግረዋል።

    ኢራን በበኩሏ በአሜሪካ ለሚከፈትባት ማንኛውም እርምጃ የምትሰጠው ምላሽ “አውዳሚ” እንደሚሆን አስጠንቅቃለች።

  16. ሄዝቦላህ በአሜሪካ ማዕቀብ ምክንያት እስራኤልን ‘መቋቋም’ እንደማያቆም አስታወቀ

    ሄዝቦላህ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የሊባኖሱ ታጣቂ ቡድን ሄዝቦላህ እስራኤልን “ለመቋቋም” የሚያደርገውን ንቅናቄ አሜሪካ ማስቆም እንደማትችል አስታወቀ።

    አሜሪካ ሄዝቦላህ ለኢራን በሚሰጠው ድጋፍ ምክንያት ማዕቀብ መጣሏን ተከትሎ ባወጣው መግለጫ ነው አቋሙን ይፋ ያደረገው።

    የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ትናንት ባወጣው መግለጫ ለሄዝቦላህ የሰጠውን ሕጋዊ ፍረጃ “በኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ቁድስ ኃይል ሥር ለኢራን መንግሥት ድጋፍ የሚሰጥ” ብሎታል።

    በተጨማሪም ለሄዝቦላህ ገንዘብ ያዘዋውራሉ በተባሉ 10 ግለሰቦች ላይ ማዕቀብ ተጥሏል።

    ሄዝቦላህ በሰጠው ምላሽ “እነዚህ ሁሉ ማዕቀቦች እና ፍትሐዊ ያልሆኑ ፍረጃዎች ከትግል መንገዳችን እና የሊባኖስን መብት፣ መሬት፣ ሉዓላዊነት እና ሃብት ለመጠበቅ ከምናደርገው ንቅናቄ አያስቆሙንም” ብሏል።

    ከኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ጋር ያለው “ቅርብ እና የወንድማማችነት ግንኙነት የሚያኮራው” እንደሆነም ቡድኑ ጠቅሷል።

    የአሜሪካ ግምጃ ቤት ሄዝቦላህ ሰዎችን በመመልመል “ከሊባኖስ፣ ቱርክ፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች እና ኢራን በሚነሱ የንግድ በረራዎች በመቶ ሚሊዮን የሚቆጠር ዶላር በተለያዩ ግዛቶች ማዘዋወሩን” ገልጿል።

  17. ቱርክ የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ላይ የእስር ማዘዣ አወጣች

    ቤንያሚን ኔታንያሁ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ቱርክ የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ላይ ዓለም አቀፍ የእስር ማዘዣ አወጣች።

    ወደ ጋዛ ሰብአዊ እርዳታ ጭኖ ሲጓዝ የነበረ መርከብ በእስራኤል በቁጥጥር ሥር ከመዋሉ ጋር በተያያዘ በሚደረግ ምርመራ ምክንያት የእስር ማዘዣው እንደወጣ ተገልጿል።

    የቱርክ የፍትሕ ሚኒስትር አኪን ጉርሌክ ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታንያሁ ላይ የእስር ማዘዣ መውጣቱን በኤክስ ገጻቸው አስታውቀዋል።

    ከአራት ወራት በፊት ከ40 አገራት የተውጣጡ ከ430 በላይ የፍልስጤም የመብት ተሟጋቾች በእስራኤል ኃይሎች በቁጥጥር ሥር መዋላቸው ይታወሳል።

    የመብት ተሟጋቾቹ በመርከብ ወደ ጋዛ ሰብአዊ እርዳታ ይዘው እየተጓዙ ነበር።

    ጋዛ ላይ የተጣለውን ዕቀባ የሚቃወም ንቅናቄ አባል የሆኑት የመብት ተሟጋቾቹ በቱርክ አውሮፕላኖች ከእስራኤል ወደ ቱርክ ተወስደዋል።

    ቱርክ ከዚህ ቀደምም በኔታንያሁ እና ሌሎችም ባለሥልጣናት ላይ የእስር ማዘዣ አውጥታለች።

    ይህም እስራኤል በጋዛ ከምትፈጽመው ድርጊት ጋር በተያያዘ “በዘር ጭፍጨፋ” ክሶች ምክንያት የወጣ የእስር ማዘዣ ነው።

  18. በመቀለ የሚካሄደው የአሸንዳ በዓል የመክፈቻ ሥነ ሥርዓት ተሰረዘ

    የአሸናዳ በዓል ላይ የታደሙ ነጭ የለበሱ ልጃገረዶች
    የምስሉ መግለጫ, ከሦስት ዓመት በፊት መቀለ ውስጥ በተካሄደው የአሸንዳ በዓል ታማሚዎች

    በትግራይ በርካታ ታዳሚ በሚገኝበት በየዓመቱ የሚከበረው የአሸንዳ ባህላዊ በዓል እንደወትሮው በመቀለ ስታዲየም ውስጥ እንደማይከበር ተገለጸ።

    የትግራይ ባህል እና ቱሪዝም ቢሮ ዛሬ እንዳስታወቀው ነገ ቅዳሜ ይካሄዳል ተብሎ የነበረው የአሸንዳ በዓል የመክፈቻ ሥነ ሥርዓት በክልሉ ውስጥ እየተጸመ ነው ባለው የድሮን ጥቃት ስጋት ምክንያት መሰረዙን ገልጿል።

    ወጣት ሴቶች በባህላዊ አልባሳት እና የልዩ የፀጉር አሠራር ተውበው በጭፈራ ለቀናት የሚያከብሩት በዓል የሆነው አሸናዳ በትግራይ እና በአማራ ክልሎች ውስጥ የሚካሄድ ነው።

    በትግራይ የሚካሄደው ሥነ ሥርዓት ባለፉት ዓመታት በርካታ ሕዝብ በሚገኝበት በመቀለ ስታዲየም በደማቅ ሥነ ሥርዓት ሲካሄድ የቆየ ሲሆን፣ በዚህ ዓመት ግን ይህ አከባበር እንደማይኖር ባለሥልጣናት ገልጸዋል።

    ባለሥልጣናት የበዓሉ ዝግጅት መሰረዙን ከመግለጻቸው በፊት በክልሉ ውስጥ በሚፈጸም የሴቶች ጥቃት ዙሪያ ተገቢው እርምጃ አልተወሰደም በሚል ጥቁር በመልበስ “ጥቁር አሸንዳ” በሚል ድምጻቸውን ለማሰማት እንቅስቃሴ ማድረግ ጀምረው ነበር።

    ይህንንም ተከትሎ የባህል እና ቱሪዝም ቢሮው ከባህላዊው ሥነ ሥርዓት ውጪ ሌሎች እንቅስቃሴዎች መደረግ እንደሌለባቸው አስጠንቅቆ ነበር።

    ባለፉት ወራት በፌደራል መንግሥቱ እና በህወሓት መሪዎች መካከል መካሰሶች፣ ግጭቶች እና ጥቃቶች መፈጸማቸውን ተከትሎ በትግራይ ክልል ጦርነት ሊቀሰቀስ ይችላል የሚል ስጋት ተፈጥሯል።

    በፌደራል መንግሥቱ የተቋቋመውን ጊዜያዊ መንግሥት አፍርሶ የክልሉን አስተዳደር ህወሓት ከተቆጣጠረ በኋላ በሁለቱ ወገኖች መካከል ያለው ውጥረት እየተካረረ ሄዶ ባለፉት ቀናት የድሮን ጥቃቶች መፈጸማቸው ተዘግቧል።

  19. ኢራን አሜሪካ ጥቃት ከከፈተች አውዳሚ ምላሽ እንደሚጠብቃት አስጠነቀቀች

    የኢራን ሚሳዔል፣ የመሪዎቿ ፎቶ እና ሰንደቅ ዓላማዋ

    የኢራን ጠላቶች የተሳሳተ ስሌት ውስጥ ገብተው ለሚወስዱት እርምጃ አውዳሚ ምላሽ ይጠብቃቸዋል ሲሉ የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ሜጀር ጄኔራል አሊ አብዱላሂ ተናገሩ።

    የጦር መኮንኑ የኢራን “የመከላከያ ኢንዱስትሪ ቀንን” በማስመለክት ባስተላለፉት የጽሁፍ መልዕክት የአገሪቱ የመከላከያ ሚኒስቴር “ወታደራዊ ቁሳቁሶችን ከማምረት ባሻገር፣ በቅርብ ዓመታት ውስጥ ጥቃቶችን የሚያስቀር የመከላከያ ኢንዱስትሪ አብዮት አካሂዷል” ብለዋል።

    ኤታማዦር ሹሙ አክለውም “የትኛውም ዓይነት የጠላት የተሳሳተ ስሌት እንዲሁም መደበኛ እና አዲስ ስጋት የተራቀቀ፣ አውዳሚ፣ የሚያስጸጽት እና የሚደመስስ ምላሽ ይሰጠዋል” በማለት አስጠንቅቀዋል።

    ይህ የከፍተኛ ወታደራዊ ባለሥልጣኑ አስተያየት የተሰነዘረው የአሜሪካ ባለሥልጣናት በኢራን ላይ የሚካሄደውን ወታደራዊ እርምጃ ወደ ምጣኔ ሀብታዊ ጫና ማዞራቸውን እየገለጹ ባለበት ጊዜ ነው።

    የአሜሪካ የገንዘብ ሚኒስትር ስኮት ቤሴንት አገራቸው በኢራን ላይ የምትጥላቸው ማዕቀቦች “በዓለም ታሪክ ትልቁ የተቀናጀ የምጣኔ ሀብት መነጠልን በማስከተል የኢራን መንግሥትን ለውድቀት ይመራዋል” ሲሉ ተናግረዋል።

  20. ኢትዮጵያ እና አሜሪካ በመከላከያ እና ደኅንነት ዘርፍ ለመተባበር መስማማታቸው ተገለጸ

    አሜሪካ መከላከያ መስሪያ ቤት የአፍሪካ ጉዳዮች ምክትል ረዳት ሚኒስትር ብራያን ጄ. ኤሊስ እና የመከላከያ ሚኒስቴር የውጭ ግንኙነት እና ወታደራዊ ትብብር ዋና ዳይሬክተር ሜጀር ጄኔራል ተሾመ ገመቹ

    የፎቶው ባለመብት, The Ministry of Foreign Affairs of Ethiopia

    የምስሉ መግለጫ, አሜሪካ መከላከያ መስሪያ ቤት የአፍሪካ ጉዳዮች ምክትል ረዳት ሚኒስትር ብራያን ጄ. ኤሊስ እና የመከላከያ ሚኒስቴር የውጭ ግንኙነት እና ወታደራዊ ትብብር ዋና ዳይሬክተር ሜጀር ጄኔራል ተሾመ ገመቹ

    ወደ አሜሪካ የተጓዘው የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ልዑክ፣ በሁለቱ አገራት መካከል “የመከላከያ እና ደኅንነት ዘርፍ አጠቃላይ ስትራቴጂካዊ ትብብር እንዲመሠረት” የሚያስችል ስምምነት መፈጸሙ ተገለጸ።

    ከአሜሪካ ጋር የተደረሰው የሁለትዮሽ የመከላከያ ስምምነት “ብሔራዊ ጥቅሞችን ማስጠበቅ” እንዲሁም “በአፍሪካ ቀንድ ቀጣና ዘላቂ ሰላምን ማረጋገጥ” ላይ የተመሠረተ መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል።

    ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዛሬ አርብ ነሐሴ 15/2018 ዓ.ም. ያወጣው መግለጫ እንደሚያስረዳው፤ በመከላከያ ሚኒስቴር የውጭ ግንኙነት እና ወታደራዊ ትብብር ዋና ዳይሬክተር ሜጀር ጄኔራል ተሾመ ገመቹ የተመራ ከፍተኛ ወታደራዊ ኃላፊዎችን ልዑክ ወደ አሜሪካ ተጉዟል።

    ልዑኩ ረቡዕ እና ሐሙስ በነበረው የአሜሪካ ቆይታ፣ ከአሜሪካ መከላከያ መሥሪያ ቤት አመራሮች ጋር “የሁለትዮሽ የጋራ ምክክሮችን” ማድረጉ ተገልጿል። ምክክሩ የተመራው በአሜሪካ መከላከያ መሥሪያ ቤት የአፍሪካ ጉዳዮች ምክትል ረዳት ሚኒስትር ብራያን ጄ. ኤሊስ እንደሆነም መግለጫው ጠቅሷል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መግለጫ “በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ወታደራዊ እና ዲፕሎማሲያዊ ትብብር ወደ አዲስ እና የላቀ ምዕራፍ ለማሸጋገር ስምምነት ላይ ተደርሷል” ብሏል። ሁለቱ አገራት የመከላከያ “ተቋማዊ ትብብርን ለማስፋፋት እና ስትራቴጂካዊ ቅንጅትን የበለጠ ለማጠናከር” ተስማምተዋል።

    የአሜሪካ እና ኢትዮጵያ “አጠቃላይ እና ስትራቴጂካዊ ትብብር” ከሚመራባቸው አምዶች አንዱ፤ “ብሔራዊ ጥቅሞችን እና የጋራ ተጠቃሚነትን ማረጋገጥ” የሚለው ነው። “የጋራ መተማመንን በማጠናከር ዘላቂ ትብብር መመሥረት” ሌላኛው የትብብሩ መሠረት እንደሆነ ተገልጿል።

    ሁለቱ አገራት ትብብራቸው “በአፍሪካ ቀንድ እና በሰፊው ቀጣና ዘላቂ ሰላም፣ ደኅንነት እና መረጋጋትን ለማረጋገጥ የሚደረጉ የጋራ ጥረቶችን ማጠናከርን” መርሆ እንዲያደርግ ተስማምተዋል ተብሏል።

    ሜጀር ጄኔራል ተሾመ ገመቹ እና ምክትል ረዳት ሚኒስትር ብራያን ጄ. ኤሊስ ስምምነት የተደረሰባቸው “ማዕቀፎችን በፍጥነት ለመተግበር” ቁርጠኝነታቸውን ማረጋገጣቸውም በመግለጫው ተጠቅሷል። “ሁለቱዮሽ የመከላከያ ግንኙነቱን ወደ የተሻለ እና ወደፊት ላይ ያተኮረ ስትራቴጂካዊ አጋርነት” እንዲሆንም መስማማታቸው ተገልጿል።

    አዲስ አበባ እና ዋሽንግተን ባለፈው ግንቦት ላይ የተፈራረሙት የሁለትዮሽ መዋቅራዊ ምክክር ማዕቀፍ ስምምነትም በተመሳሳይ ከሚያተኩርባቸው ጉዳዮች አንዱ "የመከላከያ እና ፀጥታ ትብብር" ነው።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ጌዲዮን ጤሞቲዮስ ወደ አሜሪካ ተጉዘው የፈጸሙት ይህ ስምምነት፤ “በፀጥታ ጉዳይ ትብብርን ለማጠናከር እና በጋራ የደኀንነት ጉዳዮች ዙሪያ ተሳትፎን ለማጠናከር" ምክክሮች እንዲደረጉ የሚያስችል ነበር።