የጀርመን መንግሥት በአውሮፓ እና አሜሪካ የኤርትራን መንግሥት በመቃወም የሚታወቁት ብርጌድ ንሃመዱ አባላት ናቸው በሚል የጠረጠራቸውን ሁለት
ግለሰቦች በቁጥጥር ሥር አዋለ።
የጀርመን ፌዴራል አቃቤ ሕግ ቢሮ በድረ ገጹ ላይ ባወጣው መግለጫ ሁለት የብርጌድ ንሃመዱ አባላት በመንግሥት ደጋፊዎች በዓላት እና በፖሊስ ኃይሎች ላይ አመፅ በማደራጀት ተጠርጥረው መያዛቸውን አስታውቋል።
የጀርመን ፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት መርማሪ ዳኛ ባወጣው ማዘዣ መሠረት የታሰሩት ግለሰቦች ኤርትራዊው መርሃዊ እና የጀርመን ዜግነት ያለው ትውልደ ኤርትራዊው ሽማንጉስ ናቸው።
ሁለቱ ተከሳሾች የእንቅስቃሴው አባላት በመሆናቸው ተጠርጥረው በስቱትጋርት አቅራቢያ በሳርባሩከን በፌዴራል የወንጀል ፖሊስ መያዛቸውን አቃቤ ሕግ አስታውቋል።
መርሃዊ "የሕዝብ ሰላምን በማወክ" በሚል ተከሷል።
በጽሕፈት ቤቱ መግለጫ መሠረት በጀርመን የአገር
ውስጥ አሸባሪ ድርጅት በሚል የተፈረጀው ብርጌድ ንሃመዱ የተቋቋመው እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2022 ነሐሴ ወር ሲሆን “የኤርትራን መንግሥት ለመጣል” ያለመ ዓለም አቀፍ እንቅስቃሴ ነው።
ንቅናቄው በጀርመን የኤርትራ መንግሥት ደጋፊዎች በሚያዘጋጇቸው በዓላት ላይ አመጽን መቀስቀስ ግቦቹን ለማሳካት እንደተጠቀመበት አስታውቋል።
በጀርመን የመንግሥት ተቋማት እና በፖሊስ ኃይሎች ላይ የሚፈጸመውን ጥቃት ግቦቹን ለማሳካት "ተቀባይነት ያለው መንገድ" አድርጎ እንደሚመለከተው አክሏል።
በእስር ማዘዣው መሠረት፣ የንቅናቄው አባላት በጊሰን እና ስቱትጋርት በተደረጉ በዓላት እና ሠልፎች ላይ ጥቃት በመሰንዘር ተሳታፊዎች እና የፖሊስ መኮንኖች ላይ ጉዳት አድርሰዋል።
አቃቤ ሕግ ጥቃቱ በንቅናቄው መሪዎች የተደራጀ ነው ሲል ከስሶ ይህም 'ለሕይወት አስጊ የሆነ መሣሪያ' መጠቀምን ያካትታል ብሏል።
መርሃዊ በጀርመን
የብርጌድ ንሃመዱ ዋና ጸሐፊ እንደነበር እና ሽማንጉስ የንቅናቄው ሊቀመንበር ሆኖ ማገልገሉን መግለጫው ጠቅሷል።
መርሃዊ በጊሰን ከተማ በተነሳው ሁከትም መሳተፉን የገለጸው አቃቤ ሕግ በአንድ ወቅትም የጥቃት ቡድንን መርቷል ሲል በመግለጫው ላይ ጠቅሷል።
ባለፈው ዓመት በተለያዩ የውጭ አገራት ሁከትና ብጥብጥ
አስነስቷል የተባለው የኤርትራ መንግሥት ተቃዋሚው ብርጌድ ንሃመዱ በጀርመን ሕግ መሰረት "በአገር ውስጥ አሸባሪነት"
ተፈርጇል።
በጀርመን፣
ቡድኑ ከአውሮፓውያኑ 2022 ጀምሮ ከኤርትራ መንግሥት ጋር ግንኙነት ባላቸው ፌስቲቫሎች ላይ በተቀናጁ ሁከቶች ተሳታፊ ነው በሚል
ተወንጅሏል።
አቃቤ
ሕግ በነሐሴ 2022 በጊሰን የተካሄዱ ፌስቲቫሎች እንዲሁም በመስከረም 2023 በስቱትጋርት
የነበረ የኤርትራውያን ማኅበር ስብሰባን ዋቢ አድርጓል።
በእነዚህ ዝግጅቶች ላይ የከፋ ጉዳትን ጨምሮ በርካታ የፖሊስ አባላት መቁሰላቸውን እንዲሁም በርካታ ተቃዋሚዎች መታሰራቸው
ተገልጿል።
"ብርጌድ
ንሃመዱ" ባለፉት ዓመታት በተለይም በምዕራባውያን እና መካከለኛው ምሥራቅ አገራት እየተስፋፋ እና ትኩረት እየሳበ የመጣ የኤርትራውያን የተቃውሞ እንቅስቃሴ ነበር።
የብርጌድ
ንሃመዱ ደጋፊዎች የተቃውሞ እንቅስቃሴያቸውን የጀመሩት የኤርትራ መንግሥት በተለያዩ ሀገራት የሚያዘጋጃቸውን ክብረ በዓሎች እና ዝግጅቶች
በማወክ ነው። አሜሪካ፣ ዩናይትድ ኪንግደም፣ እስራኤል፣ ካናዳ፣ ጀርመን፣ ስዊድን እና ስዊትዘርላንድ የኤርትራ መንግሥትን በሚደግፉ
ፌስቲቫሎች ላይ ረብሻ ያጋጠመባቸው አገራት ናቸው።
በእነዚህ
ረብሻዎች ወቅት የመንግሥት ደጋፊ በሆኑ እና በተቃዋሚ ኤርትራውያን መካከል በሚፈጠሩ ግጭቶች ምክንያት በተደጋጋሚ የፀጥታ ኃይሎችን
ጨምሮ በሰዎች ላይ ጉዳት ደርሷል።
በዚህ
ዓይነቱ አመጽ ላይ የተሳተፉ ኤርትራውያን በተለያዩ አገራት የፀጥታ ኃይሎች በቁጥጥር ስር ውለዋል።
በአውሮፓውያኑ
2023 በስቱትጋርት የተቀሰቀውን ረብሻ ተከትሎ 56 ሰዎች በእስር እንዲቀጡ ተደርገዋል።