የተባበሩት መንግሥታት የሆርሙዝ ወሽመጥን ለመዝጋት የሚያስችል ሕጋዊ መሠረት የለም አለ
የተባበሩት መንግሥታት ዓለም አቀፍ የማሪታይም ድርጅት፤ ማንም አገር ለዓለም አቀፍ ትራንዚት ጥቅም ላይ በሚውለው የሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚደረግ ጉዞን የማገድ ሕጋዊ መብት እንደሌለው ገለጹ።
የዓለም አቀፉ የባሕር ጉዞ ተቋም ዋና ጸሐፊ አርሴኒዮ ዶሚንጌዝ ከቢቢሲ ራዲዮ 4 ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የሚደረግ ጉዞ መታገዱ አደገኛ ምሳሌን የሚያስቀምጥ እንደሆነ ተናግረዋል።
“ግጭት እየተካሄደ እንደሆነ እረዳለሁ፤ ነገር ግን አሁንም ቢሆን ለዓለም አቀፍ ጉዞ ጥቅም ላይ የሚውልን ማንኛውም ወሽመጥ ለማገድ የሚወሰድ እርምጃ በዓለም አቀፍ ሕግ ሕጋዊ መሠረት የለውም” ብለዋል።
ዋና ጸሐፊው ዶሚንጌዝ፤ “ተጨማሪ የአጸፋ እርምጃዎች በተወሰዱ ቁጥር፤ በፋርስ ባሕረ ሰላጤ መውጫ ያጡት 20 ሺህ ባሕርተኞች እና በዓለም ዙሪያ ኢኮኖሚያዊ ተጽዕኖ የበረታባቸው ሰዎች ስጋት ይጨምራል” ሲሉም ተናግረዋል።
“ለረጅም ጊዜ በቆየ ቁጥር ተጽዕኖው በሁላችንም ላይ ለተራዘመ ጊዜ ይቆያል” ሲሉም ስጋታቸውን ገልጸዋል።
በአሜሪካ እና እስራኤል ጥቃት የተከፈተባት ኢራን ከዓለም ነዳጅ 20 በመቶው የሚተላለፍበትን የሆርሙዝ ወሽመጥ በመዝጋት የአጸፋ እርምጃ ወስዳለች።
ለእዚህ የኢራን እርምጃ ምላሽ የሰጡት የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ደግሞ በሆርሙዝ በኩል ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረግ ጉዞን ከትናንት ጀምሮ አግደዋል።