በሞቃዲሾ ለሁለት ቀናት የቆየው ግጭት ጋብ ማለቱ ተዘገበ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
የመንግሥት ወደታሮች እና የተቃዋሚ ፖለቲከኞች ደጋፊ ሚሊሻዎች ሞቃዲሾ ውስጥ ለሁለት ቀናት ከተጋጩ በኋላ የሶማሊያ የፀጥታ ኃይሎች ችግሩን በቁጥጥር ሥር ማዋላቸውን የአገሪቱ ማስታወቂያ ሚኒስቴር ገለጸ።
"የተቃዋሚ ቡድን ሚሊሻዎች ትጥቅ ፈትተው ከነበሩባቸው ቦታዎች እንዲወጡ ተደርገዋል።” ያለው ሚኒስቴሩ ግጭቱን ፈርተው የሸሹ ነዋሪዎች ወደ መደበኛ ኑሯቸው ተመልሰዋል ብሏል።
ነገር ግን ነዋሪዎች ሚሊሻዎች ትጥቃቸውን አለመፍታታቸውን እና ግጭቱም የቆመው በጎሳ መሪዎች በተደረገ የሽምግልና ጥረት መሆኑን ለሮይተርስ ተናግረዋል።
ግጭቱ የተቀሰቀሰው የሥልጣን ጊዜያቸው ካበቃ በኋላ ቦታቸውን ያላስረከቡትን ፕሬዝዳንት ሐሰን ሼክ ሞሐመድን የሚቃወም ሰልፍ ለማካሄድ የተያዘው ዕቅድ ከመተግበሩ በፊት ነው።
ባለፈው መጋቢት ወር የአገሪቱ ፓርላማ የፕሬዝዳንቱን የሥልጣን ቆይታ በአንድ ዓመት የሚያራዝመውን ሕገ-መንግሥታዊ ለውጥ በመደገፍ የምርጫ ጊዜውን በአንድ ዓመት ገፍቶታል።
ሐሙስ ዕለት የቀድሞው ፕሬዝዳንት ሻሪፍ ሼክ አህመድ የመንግሥት ኃይሎች ቤታቸውን ዒላማ ማድረጋቸውን እና መንግሥት “በሕገ- ወጥነት ሕገ መንግሥቱን አሻሽሏል” ሲሉ ከስሰዋል።
የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ሐሳን አሊ ካሂር በተመሳሳይ የመንግሥት ወታደሮች ፀረ ታንክ መሳሪያ እና ድሮኖችን ጨምሮ ከባድ መሳሪያዎችን ሕዝብ በሚበዛባቸው ቦታዎች ላይ ተጠቅመዋል ሲሉ ክስ አሰምተዋል።
የማስታወቂያ ሚኒስቴር ግን ሁለቱን የቀድሞ ባለሥልጣናት ታጣቂዎቻቸውን ወደ መኖሪያ አካባቢዎች በማሰማራት እና ፖሊሶችን እንዲያጠቁ በማድረግ የሰላማዊውን ሕዝብ ሕይወት ለአደጋ አጋልጠዋል ሲል ወቅሷል።
የተባበሩት መንግሥታት፣ የአፍሪካ ኅብረት እና የምሥራቅ አፍሪካ አገራት ማኅበር በግጭቱ ውስጥ የሚሳተፉ ወገኖች አለመግባባታቸውን በንግግር እንዲፈቱ ጥሪ አቅርበዋል።






















