የአሜሪካ ጦር ኢራንን መደብደቡን ሲቀጥል፤ ቴህራን የባሕረ ሰላጤው አገራትን ላይ የምታደርሰውን ጥቃት አስፋፋች

የፎቶው ባለመብት, centcom
አሜሪካ እሁድ ሌሊት ኢራን ውስጥ በፈጸመችው ድብደባ በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚያልፉ መርከቦችን ለማጥቃት ጥቅም ላይ ይውላል ያለችውን የሚሳዔል ክምችት መምታቷን አስታወቀች።
ለዚህ እርምጃ ምላሽ የሰጠው የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በበኩሉ ባህሬን፣ ኩዌት እና ዮርዳኖስ ውስጥ የሚገኙ የአሜሪካ የጦር ሰፈሮች ላይ በፈጸማቸው የአጸፋ ጥቃቶችን በርካታ ዒላማዎችን ማውደሙን ገልጿል።
ካለፈው ሳምንት ወዲህ በድጋሚ ያገረሸው የአሜሪካ እና ኢራን ግጭት፤ ወደ ሌላ ሳምንት ተሸጋግሯል። ቅዳሜ ዕለት አሜሪካ በመላው ኢራን የሚገኙ ከ140 በላይ ዒላማዎችን መምታቷን አስታውቃ ነበር። እንደ አሜሪካ ገለጻ ይህ ጥቃት የተፈጸመው የኢራን ኃይሎች በሆርሙዝ ወሽመጥ ይጓዙ የነበሩ መርከቦችን በማጥቃታቸው ነው።
መርከቦቹ በትክክለኛው የጉዞ መስመር ላይ እንዳልነበሩ የገለጸችው ኢራን በአንጻሩ፤ ከእሁድ ዕለት አንስቶ በድጋሚ እስኪገለጽ ድረስ የሆርሙዝ ወሽመጥ መዘጋቱን አስታውቃለች። በተጨማሪም የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በትናንትናው ዕለት በቀጣናው በሚገኙ የአሜሪካ የጦር ሰፈሮች እና አጋሮቿ ጋር ጥቃት አድርሷል።
በዚህ መልኩ ከፍ ወዳለ ደረጃ የደረሰው የሁለቱ አገራት ግጭት፤ ትናንት ሌሊትም ቀጥሏል። የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) እሁድ ሌሊት ኢራን ላይ በከፈተው አዲስ ዙር ጥቃት የቴህራንን በሆርሙዝ ወሽመጥ ጥቃት የማድረስ አቅም ይቀንሳል ያለውን ድብደባ መፈጸሙን አስታውቋል።
የአሜሪካ ኃይሎች ኢራንን አየር መከላከያ ሥርዓቶችን፣ የባህር ዳርቻ የራዳር ማዕከላትን፣ የሚሳዔል እና የድሮን አቅሞችን እንዲሁም አነስተኛ የጦር መርከቦችን ዒላማ ማድረጋቸውን ገልጿል። በዚህ ወደታራዊ ዘመቻ ላይ የአሜሪካ ተዋጊ ጄቶች፣ የባህር ኃይል መርከቦች እንዲሁም ለዚህ ዘመቻ ለመጀመሪያ ጊዜ የባሕር ኃይል አጥፍቶ ጠፊ ድሮኖች ጥቅም ላይ መዋላቸውን ዘርዝሯል።
ማዕከላዊ ዕዙ ባወጣው መግለጫ፤ “ሆርሙዝ ወሽመጥ ለዓለም አቀፍ ንግድ ወሳኝ የባሕር መተላለፊያ ነው። ኢራን አትቆጣጠረውም” ብሏል። የአሜሪካ ኃይሎች “የንግድ መርከቦችን የጉዞ ነጻነት ለማረጋገጥ ዝግጁ” መሆናቸውንም አክሏል።
በተመሳሳይ መግለጫ ያወጣው ኢራን አብዮታዊ ዘብ በኩሉ የአሜሪካ ጦር ይዞታዎችን ይዘዋል በተባሉ በቀጣናው አገራት ላይ ጥቃት ማድረሱን አስታውቋል። ባህሬን፣ ኩዌት እና ዮርዳኖስ ጥቃት የተፈጸመባቸው አገራት እንደሆኑ ተጠቅሷል።
አብዮታዊ ዘቡ፤ "ዮርዳኖስ ውስጥ በሚገኘው ፕሪንስ ሀሰን የአየር ኃይል ጦር ሰፈር በርካታ ትላልቅ የሚሳዔል ማከማቻዎች እና የነዳጅ ታንከሮች በሚሳዔል እንዲሁም ድሮን ጥቃቶች በእሳት ጋይተዋል" ብሏል።
እነዚህ ጥቃቶች የተፈጸሙት ለአሜሪካ ድብደባዎች ምላሽ ለመስጠት መሆኑን የገለጸው አብዮታዊ ዘቡ፤ ባሕሬን ውስጥ ደግሞ “ወሳኝ የአሜሪካ ጦር የሄሊኮፕተር ጥገና ማዕከላትን፣ የፒ8 የኤሌክትሮኒክስ የጦር አውሮፕላን ማቆሚያዎችን እንዲሁም የድሮን ዕዝ እና ቁጥጥር ማዕከልን” መምታቱን ገልጿል።
ለአብዮታዊ ዘቡ ቅርበት ያላቸው የዜና ወኪሎች ኩዌት ውስጥ ፍንዳታ መሰማቱን የዘገቡ ሲሆን፤ አብዮታዊ ዘቡ ባወጣው መግለጫ ፍንዳታው የአሜሪካ ጦር ሠፈር ላይ ከተፈጸመ ጥቃት ጋር የተያያዘ መሆኑን ተናግሯል።
እንደ የተጀመረው ጥቃት አሜሪካ እና ኢራን ተፈራርመውት የነበረውን የጊዜያዊ የተኩስ አቁም ስምምነት አደጋ ውስጥ ጥሎታል። ይህ ስምምነት ሆርሙዝ ወሽመጥ እንዲከፈት እንዲሁም ግጭቱ በቋሚነት እንዲቆም የማድረግ ዓላማ ነበረው።
ይሁን እንጂ አደራዳሪዎች ስምምነቱን በድጋሚ ለመመለስ ጥረት እያደረጉ መሆኑን የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ተናግረዋል።
