ቀጥታ, ሆርሙዝ ላይ ሦስት መርከቦች ጥቃት ሲፈጸምባቸው፣ ኢራን ሁለት መርከቦችን በቁጥጥር ስር አዋለች

የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በፈጸመው ጥቃት ሦስት የጭነት መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ መመታታቸውን የኢራን መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ትራምፕ ከኢራን ጋር በሚቀጥሉት ጥቂት ቀናት ሁለተኛው ዙር ድርድር ሊደረግ እንደሚችል ተናገሩ

    ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ዶናልድ ትራምፕ ከኢራን ጋር የሚደረገው ሁለተኛ ዙር የሰላም ድርድር አርብ ዕለት “ሊጀመር ይችላል" ማለታቸውን ኒውዮርክ ፖስት ዘገበ።

    ጋዜጣው የፓኪስታን ባለሥልጣናትን ጠቅሶ "ከ36 እስከ 72 ሰዓታት" ባሉት ጊዜያት ውስጥ ውይይቱ ሊጀመር እንደሚችል ዘግቧል።

    የፓኪስታን ባለሥልጣናት ያሉትን በሚመለከት የተጠየቁት ትራምፕ በጽሑፍ መልዕክት "ሊሆን ይችላል!" በማለት መልሰዋል።

    ትራምፕ ረቡዕ ዕለት የሚያበቃውን የሁለቱን አገራት የተኩስ አቁም በትናንትናው ዕለት ሲያራዝሙ የኢራን አገዛዝ ጦርነቱን ለማቆም የሚያስችል "የተቀናጀ ሀሳብ" ለማምጣት ተጨማሪ ጊዜ እንደሚያስፍለገው ተናግረው ነበር።

  2. ኢራን ምን ያህል የዩራኒየም ክምችት አላት?

    የኢራን ሳይንቲስቶች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images/BBC

    አሁኑ ባለው ድርድር ውስጥ ዋነኛው መነጋገሪያ የኢራን የበለፀገ የዩራኒየም ክምችት ምን መሆን አለበት የሚለው ነው።

    ጦርነቱ ሲጀመር ኢራን 440 ኪሎ ግራም ዩራኒየም እንዳላት እና ይህም 60 በመቶ የበለጸገ መሆኑን አንድ የአሜሪካ ባለሥልጣን ተናግረው ነበር።

    ይህም ጦር መሣሪያ ለማምረት ወደሚያስችለው 90 በመቶ የበለጸገ ዩራኒየም በአንፃራዊነት በፍጥነት ሊያድግ ይችላል።

    ኢራን በተጨማሪም 20 በመቶ ድረስ የበለጸገ 1,000 ኪሎ ግራም፣ እንዲሁም 3.6 በመቶ ገደማ የበለጸገ 8,500 ኪሎ ግራም ዩራኒየም አላት።

    ይህም በተለምዶ ለሰላማዊ አገልግሎት ማለትም ለኃይል ማመንጨት ወይም ለሕክምና ምርምር ይውላል።

    ወደ ኒውክሌር ጦር መሣሪያነት ሊቀየር የሚችለው በከፍተኛ ደረጃ የበለፀገ ዩራኒየም በአብዛኛው በኢስፋሃን እንደተከማቸ ይታመናል። ተቋሙ ባለፈው ዓመት በአሜሪካ እና በእስራኤል የአየር ድብደባ ዒላማ ከተደረጉት የኢራን ሦስት የመሬት ውስጥ የኒውክሌር ጣቢያዎች አንዱ ነው።

    ይሁን እንጂ በከፍተኛ ደረጃ ከበለፀገው ዩራኒየም ምን ያህል በሌሎች ቦታዎች እንደተከማቸ ግልጽ አይደለም።

    ምንጮች እንደሚሉት ቴህራን ለ20 ዓመት ኒውክሌር እንዳታበለጽግ የተቀመጠውን እገዳ ውድቅ አድርጋለች። በምትኩ ጦርነቱ ከመፈንዳቱ በፊት ያቀረበችውን የአምስት ዓመት ገደብ ለድርድር አቅርባለች።

    በተጨማሪም 440 ኪሎ ግራም የበለፀገውን የዩራኒየም ክምችት እንድታስረክብ የቀረበውን ጥያቄ ውድቅ አድርጋለች።

    ይህም ቀደም ሲል 60 በመቶ የበለፀገውን ዩራኒየሟን ለማዳከም በሚለው አቀወማ ጸንታለች።

    የዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ ኃላፊ ራፋኤል ግሮስ ባለፈው ዓመት በጥቅምት ወር ለኤፒ እንደተናገሩት ይህ መጠን የበለጠ ቢበለጽግ 10 የኒውክሌር ቦምቦች ለማምረት በቂ ይሆናል።

  3. የኮንዶም ዋጋ በኢራን ጦርነት ምክንያት በ30 በመቶ ሊጨምር ይችላል ተባለ

    ኮንዶም

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የዓለማችን ግዙፉ የኮንዶም አምራች ኩባንያ ካሬክስ ኃላፊ በኢራን ጦርነት ምክንያት ለምርቶቹ የሚያስፈልጉ ጥሬ ዕቃዎች አቅርቦት ማስተጓጎሉን ከቀጠለ ኩባንያው ዋጋውን እስከ 30 በመቶ ወይም ከዚያ በላይ እንደሚጨምር አስታወቁ።

    የካሬክስ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ጎህ ሚያህ ኪያት ለመገናኛ ብዙኃን እንደተናገሩት ግጭቱ ከተጀመረበት ጊዜ ጀምሮ የምርት ወጪ በከፍተኛ ሁኔታ ጨምሯል።

    ማሌዥያ የሚገኘው ይህ ኩባንያ በዓመት ከአምስት ቢሊዮን በላይ ኮንዶሞችን ያመርታል።

    ዘንድሮ የኮንዶም ፍላጎት በ30 በመቶ ገደማ ጭማሪ ያሳየ ቢሆንም የጭነት ወጪ በመጨመሩ እና የመርከብ ጉዞ መስተጓጎል እየተባባሰ በመምጣቱ እጥረት መፈጠሩን ጎህ ተናግረዋል።

    "በአስቸጋሪ ጊዜያት ኮንዶም የመጠቀም አስፈላጊነት የሚጨምረው የወደፊት ሕይወትን፣ በሚቀጥለው ዓመት ሥራ ይኖርዎት እንደሆነ እርግጠኛ ስላልሆኑ ነው" ሲሉ ለብሉምበርግ ተናግረዋል።

    "አሁን ልጅ ከወለዱ፣ ሌላ ተጨማሪ ሰው መመገብ ይኖርብዎታል" ሲል አክሏል።

  4. የሊባኖስ የተኩስ አቁምን ለማራዘም ንግግር እየተደረገ መሆኑን የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ገለጹ

    የሊባኖስ ፕሬዚዳንት ጆሴፍ አውን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የሊባኖስ ፕሬዚዳንት ጆሴፍ አውን

    የሊባኖስ ፕሬዚዳንት ጆሴፍ አውን አገራቸው ከእስራኤል ጋር የጀመረችውን የአስር ቀን “የተኩስ አቁም ስምምነት የጊዜ ገደብ ለማራዘም” ንግግር እየተደረገ መሆኑን ገለፁ።

    ሊባኖስ እና እስራኤል ሐሙስ ዕለት በዋሺንግተን ተገናኝተው ለመነጋገር ቀጠሮ ይዘዋል። በሁለቱ አገራት መካከል የአስር ቀን የተኩስ አቁም ስምምነት የተደረሰው ባለፈው ሳምንት ነበር።

    አውን በኤክስ ገጻቸው ላይ ውይይቶቹ የተዘጋጁት “የእስራኤል ጥቃት ሙሉ በሙሉ በሚቆምበት፣ እስራኤል ከሊባኖስ ግዛቶች ለቅቃ በምትወጣበት፣ እስረኞችን በመመለስ፣ በዓለም አቀፍ ድንበሮች አካባቢ ወታደሮች በማሰማራት እና በጦርነቱ የወደሙትን መልሶ በመገንባት ላይ ነው።”

    አውን የሊባኖስ አቋምን ሲናገሩ “የምንደራደርበት ግልጽ ነው፤ ከሊባኖስን ሉዓላዊነት እና ጥቅም በስተቀር ምንም ዓይነት ስምምነት፣ ድርድር፣ እጅ መስጠት አይኖርም” ብለዋል።

    ፕሬዚዳንቱ በዚሁ ልጥፋቸው ላይ ከአሜሪካ የተገኘው ድጋፍ ለሊባኖስ "ማባከን የሌለብንን ዕድል" ፈጥሮልናል ብለዋል።

  5. የነዳጅ ዋጋ በመናሩ የጀመርን አየር መንገድ 20 ሺህ በረራዎችን ሊያቆም ነው

    የሉፍታንዛ አውሮፕላኖች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በነዳጅ ዋጋ መጨመር ምክንያት የጀርመን አየር መንገድ፣ ሉፍታንዛ፣ በመጪዎቹ ወራት በአውሮፓ ውስጥ የሚያደርጋቸውን 20 ሺህ የአጭር ርቀት በረራዎችን እንደሚያቆም አስታወቀ።

    አሜሪካ እና እስራኤል ከኢራን ጋር ጦርነት ከጀመሩ በኋላ የአውሮፕላን ነዳጅ ዋጋ በእጥፍ በመጨመሩ የአጭር ርቀት በረራዎችን አክሳሪ አድርጓቸዋል።

    በዚህም ምክንያት በርካታ አየር መንገዶች በረራዎቻቸውን የቀነሱ ሲሆን፣ ሌሎች ደግሞ በትኬት ዋጋቸው ላይ ጭማሪ አድርገዋል።

    ጦርነቱ የሚካሄድበት የባሕረ ሰላጤው አካባቢ የአውሮፕላን ነዳጅ ዋነኛው ምንጭ ሲሆን፣ አብዛኛው ነዳጅም በጦርነቱ ምክንያት በተዘጋው በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚተላለፍ ነው።

    የአውሮፓ አገራት ያላቸው የአውሮፐላን ነዳጅ ክምችት እየተሟጠጠ ባለበት በአሁኑ ጊዜ፣ ክምችቱ በሳምንታት ውስጥ ሊያልቅ እንደሚችል ዓለም አቀፉ የኤነርጂ ተቋም አስጠንቅቋል።

    ሉፍታንዛ እንዳስታወቀው በአውሮፓ ውስጥ የሚያደርጋቸውን በረራዎች በከፍተኛ መጠን የሚቀንስ ቢሆንም፣ የረጅም ርቀት ዓለም አቀፍ በረራዎቹ ባሉበት ይቀጥላሉ።

    የአየር ትራንስፖርት ተንታኞች እንደሚሉት በመካከለኛው ምሥራቅ የሚካሄደው ጦርነት ከቀጠለ በአውሮፕላን ትኬት ዋጋ ላይ የበለጠ ጭማሪ እንደሚደረግ እንዲሁም በርካታ በረራዎች እንደሚሰረዙ አስጠንቅቀዋል።

  6. ኢራን ብሔራዊ ጥቅሟን ለማስከበር ‘አስፈላጊውን እርምጃ’ እንደምትወስድ ገለጸች

    ኢስማኤል ባጋይ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ኢስማኤል ባጋይ

    በኢራን እና በአሜሪካ መካከል የሚካሄደው ድርድር እየተጠበቀ ባለበት በአሁኑ ጊዜ ኢራን ብሔራዊ ጥቅሟን እንደምታስከብር አሳወቀች።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ በቴሌግራም ላይ ባሰፈሩት መልዕክት፣ አገራቸው “ብሔራዊ ጥቅሞቿን እና ደኅንነቷን ለመጠበቅ አስፈላጊ እና ተገቢውን እርምጃ ትወስዳለች” ብለዋል።

    ቃል አቀባዩ ጨምረውም ከአሜሪካ ጋር የሚደረገውን ድርደር እያሸማገለች ባለችው ፓኪስታን በኩል እየቀረበ ያለውን የተኩስ አቁም ጥያቄን በተመለከተ አገራቸው በፖለቲካው መስክ ያለው ሁኔታ “በቅርበት እየተከታተለች” መሆኗን መግለጻቸውን የኢራን የዜና ወኪል ኢርና ዘግቧል።

    ለሁለት ሳምንት የቆየው የተኩስ አቁም ሲጠናቀቅ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በኢራን ያለው መንግሥት “በከባድ ሁኔታ መፍረክረኩን” በመጥቀስ ከፓኪስታን በኩል የቀረበላቸውን ጥያቄ መቀበላቸውን አሳውቀዋል።

    ቃል አቀባዩ ባጋይ ከአሜሪካ ጋር ስለሚደረግ ቀጣይ ድርድር ተጠይቀው “ዲፕሎማሲ ብሔራዊ ጥቅም እና ደኅንነትን የማስጠበቂያ መሳሪያ ነው፤ ይህንን ለመጠቀም አስፈላጊ እና አሳማኝ ሁኔታ መኖሩን ስናረጋግጥ. . . እርምጃ እንወስዳለን” ብለዋል።

  7. ሆርሙዝ ላይ ሦስት መርከቦች ጥቃት ሲፈጸምባቸው፣ ኢራን ሁለት መርከቦችን በቁጥጥር ስር አዋለች

    በኢራን ከተያዙ የጭነት መርከቦች አንዷ

    የፎቶው ባለመብት, Agustin Alapont

    የምስሉ መግለጫ, በኢራን ከተያዙ የጭነት መርከቦች አንዷ

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በፈጸመው ጥቃት ሦስት የጭነት መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ መመታታቸውን የኢራን መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    አብዮታዊ ዘቡ እርምጃ ከወሰደባቸው ሦስት የጭነት መርከቦች መካከል ሁለቱን እንደያዘ አስታውቋል።

    በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ያለው የመርከቦች እንቅስቃሴ በኢራን እና በአሜሪካ ኃይሎች ማስጠንቀቂያ ውስጥ ባለበት ጊዜ ኢራን መመሪያዋን አልተከተሉም ባለቻቸው መርከቦች ላይ እርምጃ እየወሰደች ነው።

    ጥቃት 1:

    የዩናይትድ ኪንግደም የባሕር ትራንስፖርት ንግድ ማዕከል እንዳሳወቀው የአብዮታዊ ዘቡ “አጥቂ ጀልባ” በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ሲጓዝ በነበረ የግሪክ ኩባንያ ንብረት በሆነ ኮንቴይነሮችን በጫነት መርከብ ላይ ተኩስ ከፍቶ ከባድ ጉዳት አድርሷል።

    ጥቃት 2:

    በተጨማሪም የተለያዩ ምንጮች እንዳረጋገጡት ንብረትነቱ የዩናይትድ አረብ ኤምሬትስ የሆነ እና የፓናማን ሰንደቅ ዓላማ በሚያውለበልብ መርከብ ላይ ጥቃት ተፈጽሟል። በመርከቡ እና በሠራተኞቹ ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት አልደረሰም ተብሏል።

    ጥቃት 3:

    የባሕር ትራንስፖርት ደኅንነት ተቋም የሆነው ቫንጋርድ ለቢቢሲ እንዳሳወቀው ሌላ የፓናማን ሰንደቅ ዓላማ የሚያለውበልብ መርከብ ከሆርሙዝ ወሽመት በሚወጣበት ጊዜ የጥቃት ዒላማ ሆኗል። በጥቃቱም በመርከቡ የተለያዩ ክፍሎች ላይ ጉዳት እንደደረሰበት ተዘግቧል።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ ጥቃት ከተፈጸመባቸው ሦስት መርከቦች ሁለቱ “ፈቃድ ሳያገኙ እና የመርከብ እንቅስቃሴ መቆጣጠሪያ ሥርዓታቸውን በማጥፋታቸው” በቁጥጥር ስር ውለው ወደ ኢራን የባሕር ዳርቻ መወሰዳቸውን አስተውቋል።

  8. ትንታኔ፡ ባሕረ ሰላጤው ከ1990 ወዲሀ ያጋጠመው አስከፊ ቀውስ

    አነስተኛ ጀልባ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የኢራንእና የአሜሪካ ግጭት አሁን አደገኛ በሆነ ውጥረት ውስጥ ይገኛል። አደገኛ የሆነበት ዋናው ምክንያት ሁለቱም ወገኖች እርስ በእርሳቸው ስለማይተማመኑ ነው።

    ኢራን ዶናልድ ትራምፕ ለድንገተኛ ጥቃትጊዜ ለመግዛት በሚል የተኩስ አቁሙን አራዝመዋል የሚል እምነት አላት።

    ሌላው የአሜሪካ ባሕር ኃይል የኢራን ወደቦችን ዘግቶም ወደ ኢዝላማባድ ለሰላም ድርድር ላለመሄድ አሻፈረኝ ብላለች።

    ምንም እንኳ የተኩስ አቁሙ ላልተወሰነ ጊዜ ቢራዘምም ሁኔታው ግን የሚያረካ አይደለም።

    የሆርሙዝ የባህር ወሽመጥ ለሚንቀሳቀሱበት እጅግ በጣም ጥቂት መርከቦች በጣም አደገኛ ነው። የኢራን የጦር ጀልባዎች ለማለፍ በሚሞክሩ መርከቦች ላይ ተኩስ እየከፈቱ ነው።

    አሜሪካ ግን ጦሯ ወደ ኢራን ወደቦች ወይም ከወደቦቹ የሚመጡ ከ20 በላይ መርከቦችን መመለሱን ተናግራለች።

    ውጤቱ በኢራንም ሆነ በዓለም ኢኮኖሚላይ ከፍተኛ ጉዳት እያደረሰ ነው። ይህ ግጭት በቀጠለ ቁጥር በዓለም ኢኮኖሚ ላይ የሚኖረው ተጽእኖ እየባሰ ይሄዳል።

    እንዲሁም በባህረ ሰላጤው ውስጥ የለየለት ጦርነትን የማስነሳት አቅሙ ይጨምራል።

    አሜሪካ የኢራንን የኃይል ማመንጫ ጣቢያዎችን ለመደብደብ ብትሞክር ኢራን ደግሞ በአጎራባች የአረብ ባሕረ ሰላጤ አገሮች ላይ የአጸፋ እርምጃ ትወስዳለች።

    ይህ የባህረ ሰላጤው ቀውስ ኢራቅ ኩዌትን ከወረረችበት እአአ ከ1990 ወዲህ የተከሰተ የከፋው አለመረጋጋት ነው።

  9. ትራምፕ የተኩስ አቁሙን ካራዘሙ በኋላ በሆርሙዝ ላይ የሚንቀሳቀሱ ሦስት መርከቦች ጥቃት ተፈጸመባቸው

    የሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የሚቀዝፍ የጭነት መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ኢራን ረቡዕ ዕለት በሆርሙዝ የባህር ወሽመጥ ላይ ኮንቴይነር በጫኑ መርከቦች ላይ ጥቃት መፈጸሟ ተገለፀ።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ አባላት ረቡዕ ጠዋት ሦስት መርከቦች ላይ ጥቃት መፈጸማቸው የተገለፀ ሲሆን ይህም የአሜሪካ ፕሬዝዳንት የተኩስ አቁሙን ላልተወሰነ ጊዜ ካራዘሙ በኋላ የደረሰ ነው።

    የብሪታኒያ ጦር አካል የሆነው የዩኬ ባሕር ትራንስፖርት ማዕከል ሦስት መርከቦች ላይ ጥቃት መፈጸሙን ገልጾ አንደኛው ጉዳት እንደደረሰበት አስታውቋል።

    የዩናይትድ ኪንግደም የባህር ትራንስፖርት ማዕከል የመጀመርያው መርከብ ላይ ጥቃት ከተፈጸመ ጥቂት ሰዓታት በኋላ ሁለት መርከቦች ላይ ተኩስ እንደተከፈተ ገልጿል።

    እስካሁን ድረስ በሰው ሕይወት ላይ የደረሰ ጉዳት አልተሰማም።

    ጥቃት የተፈጸመባቸው ሁለት መርከቦች በግሪክ እና ዩኤኢ ባለቤትነት የተያዙ መሆናቸው ተገልጿል።

    የባህር ትራንስፖርት ላይ ክትትል የሚያደርገው ማዕከል በሁለቱ መርከቦች ላይ ጥቃት የፈጸመው ማን እንደሆነ ወዲያውኑ አለመታወቁን ገልጿል።

    ነገር ግን የመጀመርያው መርከብ ላይ ጥቃት የፈጸሙት የኢራን አብዮታዊ ዘብ ጀልባዎች ሁለቱ መርከቦች ላይ ጥቃት ፈጽመዋል የሚል ግምት አለ።

    የኢራን መንግሥት ጠንካራ ደጋፊዎች የተኩስ አቁሙ ከተጀመረ ወዲህ ለመጀመርያ ጊዜ ማክሰኞ ምሽት በመላ አገሪቱ ሚሳዔሎችን እና ማስወንጨፊያዎችን በአደባባይ በማሳየት ሠልፎችን አካሂደዋል።

    አሜሪካ እና እስራኤል የሚፈጽሙትን የአየር ድብደባ ካቆሙ በኋላ ኢራን ወደ እስራኤል እና የባሕረ ሰላጤው አገራት የምትተኩሳቸውን ድሮኖች እና ሚሳዔሎች አቁማለች።

    ረቡዕ ዕለት በወሽመጡ ላይ በሚንቀሳቀሱ መርከቦች ላይ የተሰነዘረው ጥቃት እና ቀደም ሲል አሜሪካ የኢራን መርከቦችን መከልከሏ ስጋቱ አሁንም በወሽመጡ ላይ መቀጠሉን ያሳያል።

    ትራምፕ አሜሪካ የኢራንን ወደቦች መዝጋት እንደምትቀጥል የተናገሩ ሲሆን ኢራን ደግሞ እርምጃው “ተቀባይነት እንደሌለው” በመግለጽ በኢዝላማባድ በሚደረገውውይይት ላይ ሳትሳተፍ ቀርታለች።

    የአብዮታዊ ጥበቃ ዘብ ረቡዕ ዕለት “በቀጣናው ውስጥ በሚገኙ ንብረቶቹ ላይ ከጠላት አስተሳሰብ በላይ ከባድ የሆነ ጥቃት እንደሚፈጽም” ዝቷል።

  10. የኢራን አማካሪ የትራምፕ የተኩስ አቁም ስምምነት 'ምንም ማለት አይደለም' አሉ

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ አማካሪ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የተኩስ አቁም ማራዘሚያ "ምንም ማለት እንዳልሆነ” እና "ለድንገተኛ ጥቃት ጊዜ ለመግዛት የሚያስችል ብልሃት" ነው ሲሉ ተናገሩ።

    ማህዲ ሞሐመድ በኤክስ ገጻቸው ላይ በፋርስ ቋንቋ ባጋሩት ጽሑፍ፣ የትራምፕ "ከበባ" መቀጠል "ከቦምብ ድብደባ የተለየ አይደለም" በማለት "ወታደራዊ ምላሽ መሰጠት አለበት" ብለዋል። አክለውም "ኢራን እርምጃ የምትወስድበት ጊዜ ደርሷል" ሲሉ ሃሳባቸውን አጠናክረዋል።

    ኢራን 20 በመቶ የዓለም ነዳጅ የሚተላለፍበትን ቁልፍ የባህር መስመር ዘግታ ለሳምንታት ከቆየች በኋላ የአሜሪካ የባህር ኃይል ወደ ቴህራን ወደቦች የሚገቡ እና የሚወጡ መርከቦች ላይ እግድ ጥሏል።

    እሁድ ዕለት ጦሩ የኢራን ባንዲራን የምታውለበልብ የጭነት መርከብ በቁጥጥር ስር አውሏል።

  11. በኢራን በጦርነቱ ምክንያት ቢያንስ ሁለት ሚሊዮን ሰዎች ሥራቸውን ማጣታቸው ተገለጸ

    በኢራን የዋጋ ግሽበትና ሥራ አጥነት በስፋት እየታየ ነው

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, በኢራን የዋጋ ግሽበትና ሥራ አጥነት በስፋት እየታየ ነው

    ኢራን ከአሜሪካ እና ከእስራኤል ጋር በተፈጠረ ጦርነት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ከፍተኛ የሆነ የሠራተኛ ቅነሳ ለማድረግ ተገድዳለች።

    ምክትል የሥራና የማኅበራዊ ዋስትና ሚኒስትሩ ጎላምሆሴይን መሐመድ ከሁለት ቀናት በፊት በጦርነቱ ምክንያት ሁለት ሚሊዮን ሰዎች ሥራቸውን አጥተዋል ብለዋል።

    ሰፊው የሠራተኞች ቅነሳ በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ በኢራናውያን መካከል ትልቅ የመነጋገሪያ ርዕሰ ጉዳይ ሆኗል።

    ተፅዕኖው የአየር ድብደባ ተፈጽሞባቸው የተዘጉ ፋብሪካዎች ብቻ የሚመለከት አይደለም። ሌሎች አምራቾችን፣ ቸርቻሪዎችን፣ የአስመጪና ላኪ ንግድ ድርጅቶችን እና ዲጂታል ዘርፉንም ጎድቷል።

    "ከባቡር ጣቢያዎች ባዶነት መመልከት ትችላላችሁ" ሲል አንድ ተጠቃሚ በኤክስ ገጹ ላይ ለጥፏል። ሌላ ግለሰብ በበኩሉ "በቢሯችን አቅራቢያ ካሉት የመኪና ማቆሚያ ቦታዎች ባዶነት ማየት ትችላላችሁ"ሲል የተፈጠረውን የሥራ አጥነት ስፋት ለመግለጽ ሞክሯል።

    "ከዋናው አውራ ጎዳና ባዶነት መረዳት ትችላላችሁ።አንድ ሰዓት ተኩል የሚፈጅብኝን በግማሽ ሰዓት ብቻ ነው የደረስኩት" ሲል ሌላ አስተያየት ሰጪ ተናግሯል።

    ጦርነቱ በሸማቾች ወጪ ላይም አሉታዊ ተጽዕኖ አሳድሯል። ብዙ ሰዎች አስፈላጊ ነገሮችን መሸመት በመተዋቸው እንደ ቱሪዝም፣ ምግብ ቤቶች እና የሸቀጣ ሸቀጥ መደብሮች ውጭ ባሉ ሌሎች የችርቻሮ ነጋዴዎች ላይ ጫና ፈጥሯል።

    የኢራን ባለሥልጣናት ጦርነቱ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ ኢንተርኔት ላይ የጣሉት ገደብ በአገሪቱ በአንፃራዊነት እያደገ ባለው የቴክኖሎጂና የዲጂታል ዘርፎች ላይም ተጽዕኖ አሳድሯል።

    ባለሥልጣናት ኢንተርኔት ለመዝጋት የወሰኑት ከደህንነት ጋር በተያያዘ ነው። ይህም ክትትል፣ ስለላ እና የሳይበር ጥቃቶችን ለመከላከል ያለመ መሆኑ ተጠቁሟል።

    የኢራን የኢንፎርሜሽን እና ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ሳታር ሀሺሚ በጥር ወር እንደተናገሩት የኢንተርኔት መቆራረጥ በየቀኑ ኢኮኖሚውን ቢያንስ 35 ሚሊዮን ዶላር ያሳጣል።

    በዚህ አሃዝ መሠረት፣ ጦርነቱ ከተጀመረበት ጊዜ ጀምሮ ለ52 ቀናት የኢንተርኔት መዘጋት የኢራንን ኢኮኖሚ ከ1.8 ቢሊዮን ዶላር በላይ አሳጥቷል።

  12. የሊባኖስ መገናኛ ብዙኃን በእስራኤል ጥቃት አንድ ሰው መገደሉን ዘገቡ

    እስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ በሚገኝ መንደር ትናንት በፈጸመችው ጥቃት በመስጊድ ላይ ጉዳት ደርሷል

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, እስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ በሚገኝ መንደር ትናንት በፈጸመችው ጥቃት በመስጊድ ላይ ጉዳት ደርሷል

    የእስራኤል ጦር በደቡብ ምሥራቅ ቤይሩት ሊታኒያ ወንዝ አካባቢ በፈጸመው ጥቃት አንድ ሰው መገደሉን አና ሁለት መቁሰላቸውን የሊባኖስ መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    የእስራኤል ወታደሮች ወደ ዋዲ አል ሳሎውቂ ለመሄድ መንገዶችን እየጠረጉ መሆኑን የዘገቡት መገናኛ ብዙኃኑ፣ በደቡብ ሊባኖስ የሚገኙ ቤቶችን እና ሱቆችን “እያፈረሱ” መሆናቸውን ጠቅሰዋል።

    በትናንትናው ዕለት የእስራኤል ጦር በሊታኒያ ወንዝ አካባቢ እና ሳሎውቂ ለሚገኙ ነዋሪዎች “የሄዝቦላህ የሽብር እንቅስቃሴ ይኖራል” በሚል ማስጠንቀቂያ ሰጥቶ ነበር።

    ባለፈው ሳምንት ሊባኖስ እና እስራኤል ለአስር ቀናት የሚቆይ የተኩስ አቁም መስማማታቸው ይታወሳል።

    ዋሺንግተን ሐሙስ ዕለት በሁለቱ አገራት መካከል የሚካሄደውን ድርድር ታስተናግዳለች።

    የተኩስ አቁሙ ስምምነቱ እስራኤል “ከታቀደ፣ ሊደርስ ከሚችል ወይም ጥቃት ሲከፈትባት ራሷን ለመከላከል የትኛውን እርምጃ የመውሰድ መብት አላት" ይላል።

    በሌላ በኩል ሊባኖስ የሄዝቦላህ እና ሌሎች “ከመንግሥት ውጪ የሆኑ ታጣቂዎች፣ ከእስራኤል በሚገኙ ዒላማዎች ላይ ጥቃት አንዳይፈጽሙ “ተጨባጭ እርምጃዎችን” መውሰድ እንዳለባት ያስቀምጣል።

    ትናንት ምሽት ሄዝቦላህ የተኩስ አቁሙን በመጣስ በሰሜን እስራኤል ወደሚገኙ ዒላማዎች ሮኬት ማስወንጨፉን ገልጿል።

    በአሜሪካ የእስራኤል አምባሳደር ይቼል ሌይተር ሄዝቦላህን የተኩስ አቁሙን በመጣስ ወንጅለውታል።

  13. የኢራን አብዮታዊ ዘብ በሆርሙዝ ወሽመጥ ኮንቴይነር የጫነ መረከብ ላይ ተኩስ መክፈቱ ተገለጸ

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ኮንቴይነር የጫነ መርከብ ላይ መተኮሱን የዩኬ የባሕር ትራንስፖርት ንግድ ማዕከል (ዩኬኤምቲኦ) አስታወቀ።

    የኢራን ጦር ጀልባ ያለምንም ማስጠንቀቂያ ኮንቴይነር የጫነ መርከብ ላይ ጥቃት ፈጽሞ ከባድ ጉዳት ማድረሱ ተገልጿል።

    በብሪታኒያ ባሕር ኃይል የሚመራው የዩኬ የባሕር ትራንስፖርት ማዕከል ጥቃቱ የተፈጸመው ከኦማን ሰሜን ምሥራቅ በሚገኝ አካባቢ መሆኑን ገልጿል።

    የአብዮታዊ ዘቡ “መሳሪያ የደገነ ጀልባ” መርከቡን ተጠግቶ ያለ ምንም የሬዲዮ ማስጠንቀቂያ ወይም ሰላምታ “ተኩስ ከፍቷል” በማለት “ከባድ ጉዳት በድልድዩ [የመርከቡ መቆጣጠሪያ] ላይ ደርሷል” ብሏል።

    በኢራን አብዮታዊ ዘብ ጥቃት የተፈጸመበት መርከብ በግሪክ ኩባንያ ባለቤትነት የተያዘ መሆኑን ቢቢሲ ማረጋገጥ ችሏል።

  14. የአሜሪካ ግምጃ ቤት ኃላፊ ቴህራን ላይ ተጨማሪ ማዕቀቦችን ለመጣል ዛቱ

    የአሜሪካ ግምጃ ቤት ኃላፊ ስኮት ቤሴንት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካ ግምጃ ቤት ኃላፊ ስኮት ቤሴንት በኤክስ ገጻቸው ላይ ኢራን በኻርግ ደሴት ያላት የነዳጅ ማጠራቀሚያ “በቀናት ውስጥ” ሙሉ በሙሉ ይሞላል በማለት “የኢራን ፍርክርኩ የወጣ የነዳጅ ጉድጓዶች ይዘጋሉ” አሉ።

    “የኢራን የባሕር ላይ ትራንስፖርት ንግድን በቀጥታ ዒላማ ማድረግ የአስተዳደሩን ዋነኛ የገቢ ምንጭ ይገድባል” ሲሉ የግምጃ ቤት ኃላፊው ተናግረዋል።

    "የቴህራን ገንዘብ የማመንጨት፣ የመንቀሳቀስ እና የመመለስ አቅሟን ስልታዊ በሆነ መልኩ ለመቀነስ በ'ኢኮኖሚ ፊውሪ' በኩል ከፍተኛውን ግፊት መተግበሩን ይቀጥላል።"

    በኢራን ንግድ ላይ የአሜሪካን ማነቆ በድብቅ ለማለፍ የሚጥር ማንኛውም ሰው ማዕቀብ ሊጣልበት ይችላል ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    በአሜሪካ እና ኢራን መካከል ለሁለት ሳምንት ያህል የቆየው የተኩሰ አቁም ከማብቃቱ በፊት ዶናልድ ትራምፕ፤ ኢራን “ወጥ የሆነ ምክረሃሳብ” እስክታቀርብ ድረስ የተኩስ አቁሙን ማራዘማቸውን አሳውቀዋል።

    በተባበሩት መንግሥታት የኢራን አምባሳደር የሆኑት አሚር ሳኢድ ቴህራን ወደቦቿ ላይ የተጣለው እገዳ ሊነሳ እንደሚችል ምልክቶችን ማየቷን ተናግረዋል። አክለውም ቀጣዩ ውይይት የሚካሄደው በወደቦቿ ላይ የተጣለው እገዳ ሲነሳ ብቻ እንደሆነ ተናግረዋል።

    ዶናልድ ትራምፕ ከሴኤንቢሲ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ኢራን ወደ ፓኪስታን ልዑካኖቿን ከመላክ ውጪ “አማራጭ የላትም” ብለዋል። አክለውም ለውጥ የማይታይ ከሆነ “በቦምብ ሊደበድቡ እንደሚችሉ” ተናግረው ነበር።

  15. የሆርሙዝ ወሽመጥ መዘጋት የአሜሪካ ነዳጅ ላይ ያለውን ፍላጎት መጨመሩን ባለሙያ ተናገሩ

    የነዳጅ ማከማቻ ጋር የቆመች መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ሰኞ ምሽት በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ድረ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሑፍ የኢራን አመራር እንደ ቴክሳስ፣ ሉዊዚያና እና አላስካ ያሉ በነዳጅ ምርታቸው የበለፀጉ የአሜሪካ ግዛቶች "በመቶዎች የሚቆጠሩ መርከቦችን" እንዲያስተናግዱ አስገድዷል ብለዋል።

    ስለ መርከቦቹ ዓይነት ግልጽ ባይደረግም፣ የመርከብ እና የንግድ ተንታኞች ለቢቢሲ ቬሪፋይ እንደተናገሩት ኢራን የሆርሙዝ የባህር ወሽመጥን መዘጋቷ ለአሜሪካ የድፍድፍ ነዳጅ ያለው ፍላጎት እንዲጨምር አድርጓል።

    የባህር ወሽመጡ የባህረ ሰላጤው ነዳጅ የሚጓጓዝበት ቁልፍ መስመር ቢሆንም፣ የካቲት 21 2018 ዓ.ም. አሜሪካ እና እስራኤል ቴህራን ላይ ጦርነት በመክፈታቸው የመርከብ እንቅስቃሴ በከፍተኛ ሁኔታ ተስተጓጉሏል።

    አስመጪዎች ከመካከለኛው ምሥራቅ በባሕር ወሽመጡ በኩል ድፍድፍ ነዳጅ ማግኘት ባለመቻላቸው አማራጭ አቅራቢዎችን ለመፈለግ ተገድደዋል።

    የባሕር ላይ ትራንስፖርትን ከሚተነትኑ ኩባንያዎች የተገኘው መረጃ እንደሚያሳየው 71 የነዳጅ ጫኝ መርከቦች ጭነት ለማጓጓዝ ወደ አሜሪካ እያመሩ ነው።

    ባለፈው ዓመት በአማካይ 27 የነዳጅ ጫኝ መርከቦች ብቻ ጭነት ለማጓጓዝ ወደ አሜሪካ አቅንተዋል።

    “ከአውሮፓና ከእስያ የመጡ ገዢዎች የአቅርቦት ክፍተቱን ለመሙላት ከአትላንቲክ ተፋሰስ የሚወጣውን ነዳጅ ከአሜሪካ ባሕረ ሰላጤ ጠረፍ ጨምሮ ተደራሽና መፍትሄ አድርገው ተመልክተውታል” ሲሉ የአርገስ ሚዲያ የገበያ መረጃ ድርጅት ኃላፊ ዴቪድ ሃይደን ተናግረዋል።

    ይህ የአሜሪካን የድፍድፍ ነዳጅ ዘይት ሽያጭ እንዲጨምር እያደረገ ያለ ይመስላል።

    የባህር ትራንስፖርት ምርምር አማካሪ የሆኑት ድሬሪ እንደሚሉት፣ በሚያዝያ 10 መጨረሻ ሳምንት የአሜሪካ የመርከብ ጭነት በቀን 5.2 ሚሊዮን በርሜል ደርሷል። ይህም በሰባት ወራት ውስጥ ከፍተኛው ነው።

  16. የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሃፊ የተኩስ አቁም መራዘሙን አደነቁ

    የመንግሥታቱ ደርጅተ ዋና ጸሃፊ አንቶኒዮ ጉታሬዝ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የመንግሥታቱ ደርጅተ ዋና ጸሃፊ አንቶኒዮ ጉታሬዝ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የተኩስ አቁሙን ለማራዘም ያሳለፉትን ውሳኔ ማድነቃቸውን ቃል አቀባያቸው ተናገሩ።

    ቃል አቀባያቸው ስቴፋኔ ጁሪክ “ግጭትን ለማስወገድ፣ እንዲሁም ለዲፕሎማሲ ወሳኝ ስፍራ መፍጠር እና በኢራን እና በዩናይድ ስቴትስ መካከል መተማመንን ለመገንባት ይህ አንዱ እርምጃ ነው” ብለዋል።

    የዋና ጸሃፊው ቢሮ አሜሪካ እና ኢራን የተኩስ አቁሙን ባለመጣስ እና በድርድሩ ላይ ገንቢ በሆነ መልኩ በመሳተፍ የተጀመረውን ጥረት እንዲቀጥሉ አበረታትቷል።

    ጉታሬዝ ፓኪስታን በሁለቱ አገራት መካከል ንግግር እንዲኖር የምታደርገውን ጥረት እንደሚደግፉ እና "ለግጭቱ ሁሉን አቀፍ እና ዘላቂ መፍትሄ የሚኖርበትን ሁኔታ ለመፍጠር እንደሚያግዝ ተስፋ አደርጋለሁ"ማለታቸውን ጁሪክ ተናግረዋል።

  17. ዶናልድ ትራምፕ ከኢራን ጋር የሚያደርጉት ድርድር እስኪጠናቀቅ ድረስ የተኩስ አቁሙ መራዘሙን አስታወቁ

    ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በፓኪስታን ጥያቄ መሠረት ከኢራን ጋር የገቡትንየተኩስ አቁም ማራዘማቸውን አስታወቁ። ትራምፕ የኢራን ወደቦች ላይ የተጣለው እገዳ እንደሚቀጥል ተናግረዋል።

    ትራምፕ የተኩስ አቁሙን መራዘም ያስታወቁት ከመጠናቀቁ አንድ ቀን ቀደም ብሎ ነው።

    የትራምፕ ውሳኔ ጦርነቱ ዳግም ይቀጥላል የሚለውን ፍራቻ ያስወገደ ሲሆን የሁለተኛው ዙር ድርድርም ቴህራን አቋሟን እስክታሳውቅ ድረስ ተራዝሟል።

    ዶናልድ ትራምፕ የተኩስ አቁሙን ማራዘማቸውን ተከትሎ ምክትላቸው ጄዲ ቫንስ ወደ ኢዝላማባድ የሚያደርጉት ጉዞ መሰረዙን የዋይት ሐውስ ባለሥልጣናት አስታውቀዋል።

    ኢራን ለትራምፕ ውሳኔ በይፋ መግለጫ ባትሰጥም ሁለቱም አገራት ያለ ስምምነት ጦረነቱን ለመቀጠል አንዳቸው ሌላኛቸው ላይ ሲዝቱ ነበር።

    ትራምፕ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት መልዕክት መሠረት በፓኪስታን ጦር አዛዥ እና ጠቅላይ ሚኒስትር ጥያቄ መሠረት እንዲሁም “የኢራን መንግሥት በከፍተኛ ሁኔታ በመፍረክረኩ” የተኩስ አቁሙ የኢራን መሪዎች እና ተወካዮች “የተቀናጀ ምክረ ሃሳብ ይዘው እስኪመጡ ድረስ” እንዲቀጥል መወሰናቸውን ተናግረዋል።

    ትራም ፕበዚሁ መልዕክታቸው ላይ የአሜሪካ ባሕር ኃይል በኢራን ወደቦች ላይ “እገዳውን እንዲቀጥል” አዝዘዋል።የተኩስ አቁሙ ኢራን ምክረ ሃሳቧን እስክታቀርብ እና ውይይቶቹ የሚያመጡት ውጤት ምንም ይሁን ምን እስኪጠናቀቅ ድረስ እንደሚቀጥል ተናግረዋል።

    ትራምፕ ከዚህ በፊት የተኩስ አቁሙን ለማራዘም ሃሳብ እንደሌላቸው ገልጸው ነበር። ምንም እንኳ ትራምፕ የኢራን ወደቦች ላይ የጣሉት እገዳ እንደሚቀጥል ቢናገሩም ከዚህ ቀደም የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ይህ “ከጦርነት ተግባር” አይተናነስም ሲሉ ኮንነውት ነበር።

    በተባበሩት መንግሥታት የኢራን ልዑክ አሜሪካ በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የጣለችው እገዳ የምታነሳ ከሆነ ንግግሩ ይቀጥላል ብለው እንደሚያምኑ ተናግረዋል።

  18. ፓኪስታን በድርድሩ ኢራን መሳተፏ እንዳልተረጋገጠ ለመጀመሪያ ጊዜ በይፋ ገለጸች

    ፓኪስታን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በአሜሪካ እና ኢራን መካከል ይደረጋል ተብሎ በሚጠበቀው ሁለተኛ ዙር ንግግር ቴህራን እንደምትሳተፍ እስካሁን በይፋ አለማሳወቋን የአሸማጋይዋ አገር ፓኪስታን ገለጸች።

    የፓኪስታን መረጃ እና ብሮድካስት ሚኒስትር አቱላህ ታራር እንደተናገሩት ፓኪስታን እንደ አሸማጋይ አገርነቷ “ከኢራን ጋር ያልተቋረጠ ግንኙነት” እያደረገች እንዲሁም "የዲፕሎማሲ እና የንግግር መንገድን እየተከተለች” ነው።

    አሜሪካ እና ኢራን የደረሱት የሁለት ሳምንት ተኩስ አቁም በነገው ዕለት የሚጠናቀቅ ሲሆን ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ተደራዳሪ ቡድናቸውን ወደ ፓኪስታን እንደሚልኩ አስታውቀዋል።

    የተኩስ አቁሙ ጊዜ ከመጠናቀቁ በፊት ኢራን በድርድሩ እንደምትሳተፍ ውሳኔ ማሳለፏ “ወሳኝ” መሆኑን የፓኪስታኑ ሚኒስትር ተናግረዋል።

    ሚኒስትሩ በኤክስ ገጻቸው ባወጡት መግለጫ፤ “ፓኪስታን የኢራን አመራሮች በሁለተኛው ዙር ድርድር እንዲሳተፉ ለማሳመን ከልብ የመነጨ ጥረት አድርጋለች፤ ይህ ጥረትም አሁንም ቀጥሏል" ብለዋል።

    ሁለተኛው ዙር ድርድር የመካሄዱ ነገር ካለው ሳምንት መጨረሻ አንስቶ እንጥልጥል ላይ የሚገኝ ሲሆን አሁን ፓኪስታን የሰጠችው መግለጫ ንግግሩ የመካሄዱ ጉዳይ በኢራን እጅ እንደሚገኝ እውቅና የሰጠ ነው። ፓኪስታን፤ ኢራን የመሳተፏ ነገር አለመረጋገጡን በይፋ ስታሳውቅ ይህ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው።

  19. ኢራን ድርድር ውስጥ ከገባች “እጇ ከቃታው ላይ” እንደማይነሳ የመንግሥት ቃል አቀባይ ተናገሩ

    የኢራን ባንዲራ የያዙ ሰልፈኞች

    የፎቶው ባለመብት, Morteza Nikoubazl/NurPhoto via Getty Images

    ኢራን ከአሜሪካ ጋር ድርድር የምታደርግ ከሆነ ንግግር ውስጥ የምትገባው “እጇን ቃታው ላይ” አድርጋ እንደሚሆን እና መከላከያ ኃይሏ “ሙሉ ዝግጁነት” እንደሚኖረው የአገሪቱ መንግሥት ቃል አቀባይ ተናገሩ።

    ከመንግሥታዊው ዜና ወኪል ‘ኢርና’ ጋር ቆይታ ያደረጉት ቃል አቀባይዋ ፋጤሜህ ሞሃጄራኒ ኢራን በፓኪስታን ዋና ከተማ ኢስላማባድ በሚካሄደው ቀጣይ ዙር ድርድር ትሳተፍ እንደሆነ ማረጋገጫም ይሁን ማስተባበያ አልሰጡም።

    “ከፊት ለፊታችን ሁለት ስትራቴጂዎች አሉ። የመጀመሪያው የጦርነት ስትራቴጂ ነው፤ ሁለተኛው ደግሞ የዲፕሎማሲ ስትራቴጂ ነው” ሲሉ ለዜና ወኪሉ ተናግረዋል።

    የኢራን ተደራደሪ ቡድን “በብሔራዊ ጥቅም ላይ ቅንጣት እንኳ አያመቻምችም” ብለዋል።

    ቃል አቀባይዋ ይህንን የአገሪቱ መንግሥት አቋም የገለጹት ሁለተኛ ዙር ድርድር ይካሄድ እንደሆነ ማረጋገጫ ባልተገኘበት ሁኔታ ውስጥ ነው።

    ተደራዳሪ ልዑካቸውን ወደ ዛሬ ፓኪስታን እንደሚልኩ ያስታወቁት የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን ተደራዳሪዎቿን ወደ ፓኪስታን “ከመላክ ውጪ አማራጭ የላትም” ብለዋል።

    በነገው ዕለት የሚጠናቀቀውን የሁለት ሳምንት ተኩስ አቁም የማራዘም ፍላጎት እንደሌላቸውም አስታውቀዋል።

  20. ትራምፕ፤ ኢራን ተደራዳሪዎቿን ወደ ፓኪስታን “ከመላክ ውጪ አማራጭ የላትም” አሉ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን ከአሜሪካ ጋር ለሚደረገው ድርድር ልዑካኗን ወደ ፓኪስታን “ከመላክ ውጪ አማራጭ የላትም” በማለት ተናገሩ።

    በምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ የሚመራው የአሜሪካ ልዑክ ከኢራን ጋር ለሚደረግ ንግግር ዛሬ ወደ ፓኪስታን የሚጓዝ ቢሆንም እስካሁን ድረስ ቴህራን ተደራዳሪዎቿን እንደምትልክ ማረጋገጫ አልሰጠችም።

    ከአሜሪካው የቴሌቪዥን ጣቢያ ሲኤንቢሲ ጋር ቃለ መጠይቅ ያደረጉት ፕሬዝዳንት ትራምፕ፤ የሚደረገው ድርድር “ከታላቅ ስምምነት ጋር ይጠናቀቃል” የሚል መተማመን እንዳላቸው ተናግረዋል።

    አሜሪካ “እየተጋፈጠች ያለችው ከጥሩ ሰዎች ጋር አይደለም” ያሉት ትራምፕ፤ ነገር ግን “ስኬታማ” ተግባር እያከናወኑ መሆኑን ጠቅሰዋል። አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረጉ ጉዞዎች ላይ የጣለችውንም እገዳ “ታላቅ ስኬት” ሲሉ ጠርተውታል።

    አሜሪካ እና ኢራን ለሁለት ሳምንት እንዲቆይ የተስማሙት ተኩስ አቁም ነገ ረቡዕ ይጠናቀቃል። ከኢራን ጋር የሚደረገው ድርድር በጥሩ ሁኔታ የሚሄድ ከሆነ ተኩስ አቁሙን ያራዝሙት እንደሆነ የተጠየቁት ትራምፕ፤ “ያንን ማድረግ አልፈልግም” ሲሉ አቋማቸውን አሳውቀዋል።

    “የቦንብ ድብደባ እንደሚኖር እጠብቃለሁ፤ ምክንያቱም ጥሩ ባህሪ ነው” ሲሉ ተናግረዋል።

    ስምምነት ላይ ለመድረስ “ብዙ ጊዜ” እንደሌለ የጠቀሱት ፕሬዝዳንቱ፤ ኢራኖች ከአሜሪካ ጋር የሚስማሙ ከሆነ “እጅግ ጥሩ ስፍራ ላይ ያርፋሉ” ብለዋል።