ቀጥታ, ኢራን ለመጀመሪያ ጊዜ ፀረ አውዳሚ መርከብ የሆነ ሚሳዔል አሜሪካ ላይ መጠቀሟን ገለጸች

ኢራን ለመጀመሪያ ጊዜ “በአሜሪካ መርከቦች ላይ ፀረ አውዳሚ መርከብ ሚሳዔል” ጥቅም ላይ ማዋሏን የአገሪቱ ጠቅላይ የብሔራዊ ደኅንነት ምክር ቤት ጸሐፊ ሞህሴን ረዛኢ ተናገሩ። የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ ትናንት እሁድ በኤክስ ገጹ ባጋራው ልጥፍ፣ በሁለት መርከቦቹ ላይ ስለተፈጸመው ጥቃት በተዘዋዋሪ ጠቅሶ ነበር።

ጭምቅ ሃሳብ

  • ኢራን ለመጀመሪያ ጊዜ ፀረ አውዳሚ መርከብ የሆነ ሚሳዔል አሜሪካ ላይ መጠቀሟን ገለጸች
  • የነዳጅ ዋጋ በሳምንት ውስጥ ከፍተኛ ጭማሪ አሳየ

የቀጥታ ሽፋን

  1. የነዳጅ ዋጋ በሳምንት ውስጥ ከፍተኛ ጭማሪ አሳየ

    አሜሪካ በኢራን ላይ ዳግም ጥቃት በመክፈቷ ያገረሸውን የጥቃት ምልልስ ተከትሎ እየጨመረ የመጣው የነዳጅ ዋጋ ዛሬ ሰኞ ከፍተኛ ደረጃ ላይ ደርሷል።

    ባለፉት ቀናት አሜሪካ እና ኢራን በፋርስ ባሕረ ሰላጤ በሚተላለፉ ግዙፍ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ላይ ጥቃት የፈጸሙ ሲሆን፣ ይህም በወሳኙ የሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚያልፉ መርከቦች ቁጥርን በከፍተኛ መጠን ቀንሷል።

    ዛሬ ጠዋት በምሥራቅ እስያ በዋለው የነዳጅ ገበያ የነዳጅ ዋጋ ባለፈው ሳምንት መጀመሪያ የአሜሪካ ጥቃት ከመጀመሩ በፊት ከነበረበት ወደ 10 ዶላር ያህል ጭማሪ አሳይቷል።

    የነዳጅ ዋጋ መተመኛ በሆነው ብሬንት የነዳጅ ዓይነት በሰኞ ጠዋት አንድ በርሜል ዋጋው ወደ 97 ዶላር ተጠግቷል።

    በኢራን እና አሜሪካ መካከል እየተካሄደ ያለው አዲሱ የወታደራዊ ግጭት ባለፈው ሳምንት ከመቀስቀሱ ቀደም ብሎ በነበሩት ቀናት በተመሳሳይ አንድ በርሜል ነዳጅ 86 ዶላር ገደማ ነበር።

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት ከፍተው ጦርነቱ በቀጠለበት ባለፉት ስድስት ወራት የነዳጅ ዋጋ እየጨመረ መጥቷል።

    ለዚህም ምክንያቱ ኢራን የተከፈተባትን ጥቃት ተከትሎ የዓለም 20 በመቶ የነዳጅ ፍጆታ የሚተላለፍበት የሆርሙዝ ወሽመጥን መዝጋቷ ነው።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ እንደተናገሩት አሜሪካ እና እስራኤል በአገራቸው ላይ "ወረራ ከመክፈታቸው በፊት ሆርሙዝ ሙሉ በሙሉ ክፍት ነበር። አሜሪካ ሕገ ወጥ እና ጨካኝ ጦርነት በመክፈቷ መደበኛው የባሕር ትራንስፖርት እንቅስቃሴ ተስተጓጉሏል" ብለዋል።

    በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ በሚተላለፉ መርከቦች ላይ በሚፈጸመው ጥቃት ምክንያት ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ለመቆም የተገደዱ ሲሆን በዚህም ምክንያት የነዳጅ እና ሌሎች ምርቶች ዋጋ ዋጋ በእጅጉ አሻቅቧል።

  2. ኢራን ለመጀመሪያ ጊዜ ፀረ አውዳሚ መርከብ የሆነ ሚሳዔል አሜሪካ ላይ መጠቀሟን ገለጸች

    ኢራን ለመጀመሪያ ጊዜ “በአሜሪካ መርከቦች ላይ ፀረ አውዳሚ መርከብ ሚሳዔል” ጥቅም ላይ ማዋሏን የአገሪቱ ጠቅላይ የብሔራዊ ደኅንነት ምክር ቤት ጸሐፊ ሞህሴን ረዛኢ ተናገሩ።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ትናንት ባወጣው መግለጫ፣ በአሜሪካ የጦር መርከቦች ላይ የባለስቲክ ሚሳዔል ጥቃት መፈጸሙን አስታውቆ ነበር። ይህ ጥቃት የተፈጸመው የአሜሪካ ጦር የኢራን ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን በመምታቱ እና በአገሪቱ ላይ የባሕር እገዳ በመጣሉ እንደሆነ ተገልጿል።

    የብሔራዊ ደኅንነት ምክር ቤት ጸሐፊው በኢራን ቴሌቪዥን ጣቢያ ባደረጉት ቃለ መጠይቅ “ከ48 ሰዓታት በፊት ለመጀመሪያ ጊዜ የኢራን ፀረ-አውዳሚ መርከብ ሚሳኤልን በአሜሪካ የጦር መርከብ ላይ ሞክረናል። ይህ ሚሳዔል ለአሜሪካውያኑ ሲኦል ፈጥሮባቸዋል፤ ሸሽተዋል” ሲሉ ተናግረዋል።

    የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ ለዚህ የኢራን ገለጻ በቀጥታ ምላሽ አልሰጠም። ይሁን እንጂ ዕዙ ትናንት እሁድ በኤክስ ገጹ ባጋራው ልጥፍ፣ በሁለት መርከቦቹ ላይ ስለተፈጸመው ጥቃት በተዘዋዋሪ ጠቅሷል።

    “ለኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ የሚተላለፈው መልዕክት ግልጽ ይሁን፤ ሁለት መርከቦቻችን ላይ ተኩስ ከከፈታችሁ፣ እጅግ ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ ኪሳራ እንጥልባችኋለን፤ ሦስት መርከቦቻችሁንም እናወድማለን” ብሎ ነበር።

    ማዕከላዊ ዕዙ አክሎም “የአሜሪካ ኃይሎችን ለመከላከል አናመነታም፤ አስፈላጊም ከሆነ የተወሰነውን እና ተጋላጭ የሆነውን የኢራን የነዳጅ ጫኝ መርከቦች ስብስብ ሙሉ በሙሉ እናወድማለን” በማለትም አስጠንቅቋል።

    አሜሪካ ቅዳሜ ዕለት በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚገኙ ሦስት ኢራን ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን መምታቷን የኢራን አብዮታዊ ዘብ ባሕር ኃይል ቅዳሜ ዕለት አስታውቆ ነበር።

    ኢራንም በምላሹ ባልተፈቀደ የሆርሙዙ መተለላፊያ በኩል ሲጓዙ ነበር እንዲሁም በሌሎች ስፍራዎች ከአሜሪካ ጋር ግንኙነት አላቸው ያለቻቸው መርከቦች ላይ ጥቃት መፈጸሟን ገልጿለች።

    ቃለ መጠይቅ የሰጡት የኢራን የብሔራዊ ደኅንነት ምክር ቤት ጸሐፊው ረዛኢ ለመርከብ ጉዞ የተከለከለ የባህር ቀጠና ስለማቋቋም ተናግረዋል። “በሚቀጥሉት ቀናት ከአሜሪካ የከበባ መስመር እስከ መጫኛ ወደቦች ያለውን ርቀት የሚያካትት አዲስ ለመርከብ ጉዞ የተከለከለ ቀጠና ይፋ እናደርጋለን” ብለዋል።

    እንደ ዋና ጸሐፊው ገለጻ ሆርሙዝ የትኛውም አቅጣጫዎች “የሚንቀሳቀስ እና ወደ ባህረ ሰላጤው ለመጓዝ ያሰበ የትኛውም መርከብ በኢራን የማዕቀብ ዝርዝር” ውስጥ ይካተታል።