ፕሬዝዳንት ትራምፕ ራት ግብዣው ላይ ተኩስ ሲከፈት “አልሰጋሁም ነበር” አሉ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
ቅዳሜ ምሽት ሲካሄድ በነበረው የጋዜጠኞች ራት ግብዣ ላይ የተከፈተው ተኩስ ፕሬዝዳንቱን እና ሌሎች ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልታናትን ዒላማ በማድረግ እንደሆነ ቢታመንም ዶናልድ ትራምፕ በወቅቱ “ሰግተው እንዳልነበረ” ተናግረዋል።
ትራምፕ ከሲቢኤስ ኒውስ ’60 ሚኒትስ’ የቴሌቪዥን ፕሮግራም ጋር ባደረጉት ቃለ መጠይቅ “አልሰጋሁም ነበር። ሕይወትን እረዳለሁ። የምንኖረው ያበደ ዓለም ውስጥ ነው” ብለዋል።
የዋይት ሀውስ ዘጋቢ ጋዜጠኞች ራት ግብዣ ላይ የተፈጠረው ክስተት ፕሬዝዳንት ትራምፕ ላይ እንደተቃጣ ሦስተኛ የግድያ ሙከራ ተወስዷል። ሐምሌ 2016 ዓ.ም. ፔንስልቬኒያ ውስጥ የምርጫ ቅስቀሳ በሚያደርጉበት ሰዓት እንዲሁም ባለፈው መስከረም ላይ በጎልፍ ክለባቸው ውስጥ የግድያ ሙከራ ተደርጎባቸዋል።
ምክትል ፕሬዝዳንቱ ጄዲ ቫንስ በመጀመሪያ እንዲወጡ የተደረገበት የቅዳሜው ጥቃት እንዴት እንደተከሰተ ትራምፕ ተጠይቀዋል። ፕሬዝዳንቱ የሴክሬት ሰርቪስ አባላት ከክፍሉ እንዲያስወጧቸው ሁኔታዎች “ቀላል እንዳላደረጉ” በመጥቀስ ምላሽ ሰጥተዋል።
“ምን እንደተፈጠረ መመልከት ፈልጌ ነበር… ምን እየተካሄደ መሆኑን ማየት ፈልጌ ነበር። ሁኔታውን በተገነዘብኩበት ሰዓት፤ ምናልባትም መጥፎ ሁኔታ ነበር” ብለዋል።
ከክፍሉ ሲወጡ “እንዲያጎነብሱ” ስለመደረጉ የተነሳላቸው ትራምፕ፤ “[ከደኅንነት አባላት ጋር] መራመድ ጀመርኩ። ዞርኩ፣ መራመድ ጀመርኩ፤ ከዚያም ‘እባክህ አጎንብስ፣ እባክህ ወደ ወለሉ አጎንብስ’ አሉኝ” በማለት ሁኔታውን ገልጸዋል።
“ስለዚህ አጎነበስኩ፤ ቀዳማዊት እመቤቷም አጎነበሰች” ሲሉም አክለዋል።
በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ኒውስ ከተጠርጣሪው ኮል አለን ጋር ግንኙነት እንዳለው የሚታመን በእጅ የተጻፈ ሰነድን ተመልክቷል። ሰነዱ፤ “ከከፍተኛ ደረጃ እስከ ታች” ያሉ የትራምፕ አስተዳደር አባላትን ዒላማ ማድረግ እንደሚፈልግ ያሳያል።
ጽሑፉ ላይ “የህጻናት ወሲብ ጥቃት ፈጻሚ፣ ደፋሪ እና ከሃዲ” በሚል ስለሰፈሩት አገላለጾች በቃለ መጠይቁ በተነሳበት ወቅት በትራምፕ እና በጋዜጠኛዋ ኖራህ ኦ’ዶኔል መካከል ውጥረት ተስተውሎ ነበር።
ጋዜጠኛዋ ስለ እነዚህ አገላለጾች በመጠየቋ “ወራዳ” ሲሉ ጠርተዋታል። “ይህንን በማንበብሽ ልታፍሪ ይገባል፤ ምክንያቱም እኔ ከእነዚህ ነገሮች አንዱንም አይደለሁም” ብለዋል።



