ኢራን ለአሜሪካ የስምምነት እቅድ የሰጠሁት ምላሽ “ምክንያታዊ እና ለጋስ” ነው አለች
የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ቴህራን በአሜሪካ ለቀረበው የድርድር ዕቅድ የሰጠችው ምላሽ “ምክንያታዊ እና ለጋስ” እንደሆነ በመግለጽ፤ አሜሪካን ግን “ለአንድ ወገን ያደላ እና ምክንያታዊ ያልሆነ” አቋም ላይ ጸንታለች የሚል ክስ አቀረቡ።
ኢራን ባለፈው ሳምንት በአሜሪካ ለቀረበው የድርድር ዕቅድ በአሸማጋይዋ ፓኪስታን በኩል ምላሽ መስጠቷን ያሳወቀችው ትናንት እሁድ ነበር። የቴህራን ምላሽ ያላስደሰታቸው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ “ፈጽሞ ተቀባይነት የሌለው” በማለት ውድቅ አድርገውታል።
የኢራን ዜና ወኪል ዘገባ እንደሚያሳየው ቴህራን የሰጠችው ምላሽ በሁሉም ግንባሮች የሚካሄዱ ውጊያዎች እንዲቆሙ እና አሜሪካ በኢራን ወደቦች ላይ የጣለችው እገዳ እንዲነሳ ይጠይቃል። ወደፊት ኢራን ላይ ጥቃት እንደማይፈጸም ዋስትና የመስጠት ጉዳይም ምላሹ ውስጥ ተካትቷል።
ዛሬ ሰኞ ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡት የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ ኢስማኢል ባቃኢ፤ ቴህራን "ከሕጋዊ መብቶቿ" ውጭ የሆነ ጥያቄ እንዳላቀረበች ተናግረዋል።
እንደ ቃል አቀባዩ ገለጻ የኢራን ምላሽ “በቀጣናው የሚደረገው ጦርነት እንዲያበቃ”፣ “የባህር ላይ እገዳ ተብሎ የሚገለጸው በኢራን መርከቦች ላይ የሚፈጸመም የባህር ውንብድና እንዲቆም” እንዲሁም “በውጭ ባንኮች የታገደውና የኢራን ሕዝብ ንብረት የሆነው ሀብት እንዲለቀቅ” የሚጠይቅ ነው።
ቃል አቀባዩ፤ “እንዲሁም በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል አስተማማኝ የባህር ጉዞ እንዲኖር ያቀረብነው ሐሳብ ከመጠን ያለፈ ጥያቄ ነውን? ሊባኖስን ጨምሮ በመላው ቀጠናው ሰላም እንዲሰፍን መጠየቅስ እንዴት እንደ ከልክ ያለፈ ጥያቄ ሊታይ ይችላል?” በማለት ጠይቀዋል።
በእቅዱ ውስጥ የተካተቱት ነጥቦች "ምክንያታዊ እና ለጋስ" መሆናቸውን የተናገሩት ባቃኢ፤ በአንጻሩ ግን አሜሪካ "ምክንያታዊ ያልሆኑ ጥያቄዎችን" እያቀረበች ነው ሲሉ ከስሰዋል።
ፓኪስታን ውስጥ በተደረገው የመጀመሪያው ዙር ድርድር ሁለቱን አገራት ያላስማማቸው ዋነኛ ጉዳይ የኢራን የኒውክሌር ፕሮግራም ነበር።
ከዚህ ቀደም ኢራን የኒውክሌር ጉዳይ ለጊዜው ወደ ጎን ተደርጎ በቅድሚያ ጦርነቱን ማቆም እና ሆርሙዝን መክፈትን የተመለከተ ንግግር እንዲደረግ የሚጠይቅ እቅድ አቅርባ የነበረ ቢሆንም፤ አሜሪካ አልተቀበለችውም።