ቀጥታ, ኢራን ለአሜሪካ የስምምነት እቅድ የሰጠሁት ምላሽ “ምክንያታዊ እና ለጋስ” ነው አለች

የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ቴህራን በአሜሪካ ለቀረበው የድርድር ዕቅድ የሰጠችው ምላሽ “ምክንያታዊ እና ለጋስ” እንደሆነ በመግለጽ፤ አሜሪካን ግን “ለአንድ ወገን ያደላ እና ምክንያታዊ ያልሆነ” አቋም ላይ ጸንታለች የሚል ክስ አቀረቡ።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ኢራን ለአሜሪካ የስምምነት እቅድ የሰጠሁት ምላሽ “ምክንያታዊ እና ለጋስ” ነው አለች

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ቴህራን በአሜሪካ ለቀረበው የድርድር ዕቅድ የሰጠችው ምላሽ “ምክንያታዊ እና ለጋስ” እንደሆነ በመግለጽ፤ አሜሪካን ግን “ለአንድ ወገን ያደላ እና ምክንያታዊ ያልሆነ” አቋም ላይ ጸንታለች የሚል ክስ አቀረቡ።

    ኢራን ባለፈው ሳምንት በአሜሪካ ለቀረበው የድርድር ዕቅድ በአሸማጋይዋ ፓኪስታን በኩል ምላሽ መስጠቷን ያሳወቀችው ትናንት እሁድ ነበር። የቴህራን ምላሽ ያላስደሰታቸው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ “ፈጽሞ ተቀባይነት የሌለው” በማለት ውድቅ አድርገውታል።

    የኢራን ዜና ወኪል ዘገባ እንደሚያሳየው ቴህራን የሰጠችው ምላሽ በሁሉም ግንባሮች የሚካሄዱ ውጊያዎች እንዲቆሙ እና አሜሪካ በኢራን ወደቦች ላይ የጣለችው እገዳ እንዲነሳ ይጠይቃል። ወደፊት ኢራን ላይ ጥቃት እንደማይፈጸም ዋስትና የመስጠት ጉዳይም ምላሹ ውስጥ ተካትቷል።

    ዛሬ ሰኞ ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡት የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ ኢስማኢል ባቃኢ፤ ቴህራን "ከሕጋዊ መብቶቿ" ውጭ የሆነ ጥያቄ እንዳላቀረበች ተናግረዋል።

    እንደ ቃል አቀባዩ ገለጻ የኢራን ምላሽ “በቀጣናው የሚደረገው ጦርነት እንዲያበቃ”፣ “የባህር ላይ እገዳ ተብሎ የሚገለጸው በኢራን መርከቦች ላይ የሚፈጸመም የባህር ውንብድና እንዲቆም” እንዲሁም “በውጭ ባንኮች የታገደውና የኢራን ሕዝብ ንብረት የሆነው ሀብት እንዲለቀቅ” የሚጠይቅ ነው።

    ቃል አቀባዩ፤ “እንዲሁም በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል አስተማማኝ የባህር ጉዞ እንዲኖር ያቀረብነው ሐሳብ ከመጠን ያለፈ ጥያቄ ነውን? ሊባኖስን ጨምሮ በመላው ቀጠናው ሰላም እንዲሰፍን መጠየቅስ እንዴት እንደ ከልክ ያለፈ ጥያቄ ሊታይ ይችላል?” በማለት ጠይቀዋል።

    በእቅዱ ውስጥ የተካተቱት ነጥቦች "ምክንያታዊ እና ለጋስ" መሆናቸውን የተናገሩት ባቃኢ፤ በአንጻሩ ግን አሜሪካ "ምክንያታዊ ያልሆኑ ጥያቄዎችን" እያቀረበች ነው ሲሉ ከስሰዋል።

    ፓኪስታን ውስጥ በተደረገው የመጀመሪያው ዙር ድርድር ሁለቱን አገራት ያላስማማቸው ዋነኛ ጉዳይ የኢራን የኒውክሌር ፕሮግራም ነበር።

    ከዚህ ቀደም ኢራን የኒውክሌር ጉዳይ ለጊዜው ወደ ጎን ተደርጎ በቅድሚያ ጦርነቱን ማቆም እና ሆርሙዝን መክፈትን የተመለከተ ንግግር እንዲደረግ የሚጠይቅ እቅድ አቅርባ የነበረ ቢሆንም፤ አሜሪካ አልተቀበለችውም።

  2. ሦስት ድፍድፍ ነዳጅ የጫኑ ግዙፍ መርከቦች መከታተያቸውን በማጥፋት የሆርሙዝ ወሽመጥን ማቋረጣቸውን ሮይተርስ ዘገበ

    ባለፈው ሳምንት ሦስት ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ራሳቸውን ከኢራን ጥቃት ለመከላከል የመከታተያ መሣሪያቸውን በማጥፋት ወሽመጡን ማቋረጣቸውን ሮይተርስ ዘገበ።

    ሮይተርስ የመርከቦች እንቅስቃሴን ከሚከታተሉት ኬፕለር እና ኤልኤስኢጂ ያገኘውን መረጃ ጠቅሶ እንደዘገበው ሁለት ግዙፍ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ሆርሙዝን ያቋረጡት ትናንት እሁድ ነው።

    አንዱ መርከብ ግን ከአምስት ቀን በፊት ማቋረጡን የመርከቦችን እንቅስቃሴ የሚከታተሉትን ድርጅቶች ጠቅሶ ዘግቧል።

    አጊዮስ ፋኖውሪየስ I እና ኪያራ ኤም የተሰኙት መርከቦች እያንዳንዳቸው ሁለት ሚሊየን በርሜል ነዳጅ መጫናቸው ተግለጿል።

    አጊዮስ ፋኖውሪየስ I ወደ ቬይትናም የሚያመራ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን ከዚህ ቀደም ሁለቴ ወሽመጡን ለማቋረጥ ያደረገው ሙከራ ሳይሳካ ቀርቷል።

    አጊዮስ ፋኖውሪየስ I የሚያስተዳድረው ኢስተርን ሜዲትራኒያን ማሪታይም ስለመርከቡ ጉዞ አስተያየት ከመስጠት ተቆጥቧል።

    እሁድ ዕለት ወሽመጡን ያቋረጠው ሌላው ነዳጅ ጫኝ መርክ ኪያራ ኤም የጫነውን ነዳጅ ወዴት እንደሚያጓጉዝ አልታወቀም። መርከቡን የሚያስተዳድረው መቀመጫውን ሻንጋይ ያደረገው ኩባንያ ሲሆን ስለ መርከቡም ሆነ ስለ ጭነቱ የቀረበለትን ጥያቄ ሳይመልስ መቅረቱን ሮይተርስ ዘግቧል።

    ቀደም ብሎ ከአቡዳቢ ብሔራዊ የነዳጅ ኩባንያ 2 ሚሊዮን በርሜል ነዳጅ የጫነ መርከብ እአአ ግንቦት 6 የመከታተያ መሣሪያውን በማጥፋት አቋርጧል።

    አሜሪካ እና ኢራን ከሁለት ወር በፊት የገቡበት ጦርነትን ተከትሎ የሆርሙዝ ወሽመጥ በመዘጋቱ የነዳጅ፣ ጋዝ፣ ፔትሮል፣ ፕላስቲክ እና የምግብ ዋጋ ንሯል።

  3. ከኢራን ጦርነት በቢሊዮን ዶላር ትርፍ ያገኙት እነማን ናቸው?

    የካቲት መጨረሻ የተጀመረው የኢራን ጦርነት በመላው ዓለም ተጽዕኖው ተሰምቷል። በአንጻሩ ጦርነቱ በረከት የሆነላቸው ኩባንያዎች እና ዘርፎችም አሉ። የነዳጅ አከፋፋይ ኩባንያዎች በዚህ ጦርነት ትርፍ ካጋበሱት መካከል ናቸው።

    ከዓለም የነዳጅ እና የጋዝ ጭነት አንድ አምስተኛ ያህሉ የሚጓጓዝበት የሆርሙዝ ወሽመጥ፤ ከየካቲት መጨረሻ ጀምሮ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ተዘግቷል።

    ይህንን ተከትሎ የአውሮፓ የነዳጅ ኩባንያዎች ከፍተኛ ትርፍ አጋብሰዋል። በወሽመጡ መዘጋት ምክንያት የዋጋ ጭማሪ በማድረግ ከፍተኛ የሚባል ትርፍ አግኝተዋል።

    'ቢፒ' የተባለው የብሪታኒያ የነዳጅ ኩባንያ በ2026 የመጀመሪያዎቹ ሦስት ወራት ትርፉ ከእጥፍ በላይ አድጎ 3.2 ቢሊዮን ዶላር ደርሷል።

    ሌላኛው የነዳጅ ኩባንያ 'ሼል' ደግሞ በመጀመሪያው ሩብ ዓመት 6.92 ቢሊዮን ዶላር በማግኘት ተንታኞች ከጠበቁት በላይ ትርፍ አስመዝግቧል።

    ግዙፉ ዓለም አቀፍ ኩባንያ 'ቶታል ኤነርጂስ’፣ በነዳጅ እና በኢነርጂ ገበያ ዋጋ መናር ምክንያት ትርፉ በአንድ ሦስተኛ ገደማ ጨምሯል። በሦስት ወራት ውስጥ ያገኘው ትርፍም 5.4 ቢሊዮን ዶላር እንደሆነ አስታውቋል።

    በአንጻሩ የአሜሪካዎቹ ኩባንያዎች 'ኤክሶንሞቢል' እና 'ቼቭሮን' በመካከለኛው ምሥራቅ የነዳጅ አቅርቦት መስተጓጎል ምክንያት ገቢያቸው ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ጊዜ ጋር ሲነጻጸር ዝቅ ብሎ ቢታይም፤ ያገኙት ትርፍ ከባለሙያዎች ግምት የበለጠ ነው።

    የነዳጅ ዋጋ ጦርነቱ ከመጀመሩ በፊት ከነበረው በእጅጉ የጨመረ በመሆኑ፤ የሁለቱም ኩባንያዎች ትርፍ እያደገ እንደሚሄድ ይጠበቃል።

  4. ኔታንያሁ እስራኤልን ከአሜሪካ ድጋፍ ማላቀቅ እንደሚፈልጉ ለሲቢኤስ ተናገሩ

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ አገራቸውን ከአሜሪካ ወታደራዊ ድጋፍ ለማላቀቅ እንደሚፈልጉ ተናገሩ።

    ኔታንያሁ እሁድ ዕለት ከሲቢኤስ ጋር በነበራቸው ቃለ ምልልስ ወቅት በሚቀጥሉት አስርት ዓመታት ከባሕረ ሰላጤው አገራት ጋር ያላቸውን ግንኙነት በማጠናከር ከአሜሪካ የሚያገኙትን ወታደራዊ ድጋፍ ለመቀነስ ጥረት እንደሚያደርጉ ተናግረዋል።

    ኔታንያሁ ለሲቢኤስ ኒውስ "60 ደቂቃ" ፕሮግራም እንደተናገሩት "የአሜሪካን የገንዘብ ድጋፍ፣ ባለን ወታደራዊ ትብብር ላይ ያለው የገንዘብ ድጋፍን፣ ወደ ዜሮ ማውረድ እፈልጋለሁ” ብለዋል።

    ኔታንያሁ እንዳሉት እስራኤል በዓመት 3.8 ቢሊዮን ዶላር የአሜሪካን ወታደራዊ እርዳታ ታገኛለች። ዩናይትድ ስቴትስ እአአ ከ2018 እስከ 2028 በድምሩ 38 ቢሊዮን ዶላር ወታደራዊ ድጋፍ ለእስራኤል ለመስጠትተስማምታለች።

    የዩናይትድ ስቴትስ እና የእስራኤል የገንዘብ ድጋፍ ትብብር ለመለወጥ “ፍጹም” ትክክለኛው ጊዜ ነው ሲሉ ኔታንያሁ ተናግረዋል። ቀጣዩ ምክር ቤት እስኪመጣ ድረስ "መቆየት አልፈልግም” ያሉት ኔታንያሁ፣ “አሁን መጀመር እፈልጋለሁ” ብለዋል።

    እስራኤል ለረዥም ዓመታት በሁለቱም ፓርቲዎች የሥልጣን ዘመን ጠንካራ ወታደራዊ ድጋፍ ስታገኝ ቆይታለች። ነገር ግን በ2016 ዓ.ም. የጋዛ ጦርነት መቀስቀሱን ተከትሎ ከአሜሪካ ሕግ አውጪዎች እና ሕዝብ የሚገኘው ድጋፍ እየቀነሰ መትቷል።

    በመጋቢት ወር የተሰበሰበ የሕዝብ አስተያየት እንደሚያሳየው 60 በመቶ አሜሪካውያን ለእስራኤል አሉታዊ አስተያየት ያላቸው ሲሆን፤ 59 በመቶ ዎቹ በቤንያሚን ኔታንያሁ ላይ ያላቸው እምነት ዝቅተኛ መሆኑን ተናግረዋል።

  5. ቻይና ቴህራን ላይ የሚጣል ማዕቀብ ኩባንያዎቼን ይጎዳል በሚል ተቃወመች

    አሜሪካ መቀመጫቸውን ቻይና ባደረጉ ሦስት ኩባንያዎች ላይ የጣለችውን ማዕቀብ ቤይጂንግ ተቃወመች።

    ቤይጂንግ ተቃውሞዋን ያሰማችው ኩባንያዎቹ የኢራንን ወታደራዊ እንቅስቃሴ ደግፈዋል በሚል ውንጀላ ከቀረበባቸው በኋላ ነው።

    ሰኞ ዕለት ጠንካራ ተቃውሞዋን የገለጸችው ቤይጂንግ ማዕቀቦቹን ሕገ ወጥ እና የአንድ ወገን ውሳኔ ብላ ጠርታዋለች።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ የሆኑት ጉኦ ጂያኩን “ምንጊዜም የቻይና ኩባንያዎችን ሥራቸውን በሕግ እና መመሪያዎች መሠረት እንዲያከናውኑ እናደርጋለን፤ እንዲሁም የቻይና ኢንተርፕራይዞችን ሕጋዊ መብቶች እና ጥቅሞች በጽኑ እንጠብቃለን” ሲሉ ተናግረዋል።

    "ሌሎች አገራትን በስህተት ከመኮነን እና ከመተቸት አንገብጋቢው እና ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ ጦርነቱ ዳግም እንዳይጀመር መከላከል ነው” ብለዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከዢ ጂንፒንግ ጋር ለመገናኘት በዚህ ሳምንት ወደ ቻይና ያመራሉ። ከግንቦት 5 እስከ 7 2018 ዓ.ም. የሚቆየው ይህ ጉብኝት በአስር ዓመታት ውስጥ አንድ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ወደ ቻይና የሚያደርጉት የመጀመሪያው ጉዞ ይሆናል ተብሏል፡፡

  6. ትራምፕ የኢራንን የሰላም ዕቅድ ውድቅ ካደረጉ በኋላ የነዳጅ ዋጋ ጨመረ

    ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን ለአሜሪካ የሰላም ዕቅድ የሰጠችውን ምላሽ ውድቅ ካደረጉ በኋላ የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ አሳየ።

    ቴህራን ምላሹን የሰጠችው በአደራዳሪዋ ፓኪስታን በኩል ሲሆን ግጭቱ ወዲያውኑ እንዲቆም እንዲሁም ከዚህ በኋላ ምንም ዓይነት ጥቃት እንደማይፈጸምባት ማረጋገጫ እንዲሰጣት መጠየቋን ታስኒም የዜና ወኪል ዘግቧል።

    ሰኞ ዕለት ብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ በእስያ ገበያ በበርሜል የ4.1 በመቶ ጭማሪ በማሳየት 105.50 ዶላር ተሸጧል።

    የዓለም 20 በመቶ ነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ መተላለፊያ የሆነው ሆርሙዝ ከየካቲት የመጨረሻ ሳምንት ጀምሮ በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ጦርነት በመቀስቀሱ ዝግ ሀኗል።

    ጦርነቱ ከጀመረ ጊዜ አንስቶ የዓለም የነዳጅ ዋጋ በከፍተኛ ደረጃ እየጨመረ የመጣ ሲሆን የብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ በበርሜል ከ100 ዶላር በላይ እየተሸጠ ይገኛል።

    የዓለም አንድ አምስተኛው ነዳጅ የሚተላለፍበት የሆርሙዝ ወሽመጥ ከተዘጋ በኋላ ቴህራን ለማቋረጥ የሚሞክሩ መርከቦች ላይ ጥቃት እንደምትፈጽም በመግለጽ አስጠንቅቃለች።

    ጦርነቱ ከተጀመረበት የካቲት 21/ 2018 ዓ.ም. ጀምሮ እስከ ግንቦት ድረስ የሆርሙዝ ወሽመጥን ለማቋረጥ የሞከሩ 26 የነዳጅ እና ኮንቴይነር ጫኝ መርከቦች ላይ ጥቃት መፈጸሙ ተገልጿል።

    መርከቦቹ ላይ ጥቃት የደረሰው በተወንጫፊዎች፣ በአነስተኛ ጀልባዎች፣ በቦምብ ሲሆን አብዛኞቹ ጥቃቶች የተፈጸሙት ከኦማን የባሕር ዳርቻ ወጣ ባለ ስፍራ እንዲሁም የዩኤኢ ፉጃይራህ ወደብ አቅራቢያ ነው።

    ዓለም አቀፉ የባሕር ላይ ትራንስፖርት ድርጅት በሆርሙዝ ወሽመጥ ከ1500 እስከ 2000 መርከቦች እንዲሁም 20 ሺህ ባህረተኞች መንቀሳቀሻ አጥተው መቆማቸውን አስታውቋል።

    ዋና ዋና የኢነርጂ ኩባንያዎች የዓለም የነዳጅ እና የጋዝ ዋጋ ጭማሪ ማሳየቱን ተከትሎ ትርፋቸው መጨመሩን ይፋ አድርገዋል።

    እሁድ ዕለት አራምኮ ባለፉት ሦስት ወራት ያገኘው ትርፍ ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ጊዜ ጋር ሲነጻጸር የ25 በመቶ ጭማሪ ትርፍ ማግኘቱን አስታውቋል።

    ባለፈው ወር እንዲሁ ቢፒ የመጀመሪያዎቹ ሦስት ወራት ትርፉ ከእጥፍ በላይ መጨመሩን የገለጸ ሲሆን ሼል ደግሞ ባለፈው ሳምንት ትርፉ ከፍ ማለቱን ተናግሯል።

  7. ኢራን በወሽመጡ ላይ የሚሰማሩ የፈረንሳይ እና የብሪታኒያ ባሕር ኃይሎችን አስጠነቀቀች

    ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የፈረንሳይ ወይም የብሪታኒያ ባሕር ኃይሎች የሚሰማሩ ከሆነ “ወሳኝ እና ፈጣን ምላሽ” እንደምትሰጥ አስጠነቀቀች።

    የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ማክሮን አገራቸው በወሽመጡ ላይ የባሕር ኃይሏን ለማሰማራት “ዕቅድ እንደሌላት” ገልጸው ነገር ግን “ከኢራን ጋር በመተባበር” የደህንነት ተልዕኮ የሚሰጠው ጦር እንደሚሆን ተናግረዋል።

    ቅዳሜ ዕለት የብሪታኒያ ባሕር ኃይል በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የሚኖርን የመርከቦች እንቅስቃሴ ለመከላከል የሚደረግ ዓለም አቀፍ ተልዕኮ ላይ ለመሳተፍ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ የጦር መርከቡን መላኩን አስታውቋል።

    የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር እና የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት በጋራ በመሆን ጦርነቱ ካበቃ በኋላ ይጀመራል የተባለውን ይህንን ዓለም አቀፍ ተልዕኮ ደግፈው ተናግረዋል።

    ሰኞ ዕለት ከ40 አገራት በላይ የሚውጣጡ የመከላከያ ሚኒስትሮች በዩኬ የበላይነት የሚመራውን እና በወሽመጡ ላይ የሚደረግ የመርከብ እንቅስቃሴን የመከላከል ዘመቻ ዕቅድ ላይ ተገናኝተው ይወያያሉ ተብሎ ይጠበቃል።

    የዩኬው ኮን ሄይሊ እና የፈረንሳዩ አቻቸው ካትሪን ቫውትሪን በጋራ በመሆን ስብሰባውን የሚመሩ ሲሆን ጦርነቱ ከቆመ በኋላ በወሽመጡ ላይ የሚደረጉ የመርከብ እንቅስቃሴዎችን እንዴት እንደሚጠብቁ ይመካከራሉ ተብሏል።

    ቴህራን የዓለም አንድ አምስተኛ የነዳጅ ዘይት እና የተፈጥሮ ጋዝ የሚጓጓዝበትን መስመር አሜሪካ እና እስራኤል ጦርነት ከከፈቱባት የካቲት 21/2018 ዓ.ም. ጀምሮ ሙሉ በሙሉ ዘግታዋለች።

    የኢራን ጦር ቃል አቀባይ ሞሐመድ አክራሚኒያ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚያልፉ መርከቦች ከቴህራን ጋር በቅድሚያ የማይተባበሩ ከሆነ “ከባድ እርምጃ” እንደሚወሰድባቸው ማስጠንቀቃቸውን የኢርና የዜና ወኪል ዘግቧል።

    አክራሚኒያ አክለውም አሜሪካኖች “ይህንን በሰሜን ሕንድ ውቅያኖስ የሚገኝ ሰፊ የባሕር ክፍል በጦር መርከቦቻቸው ቢሞሉት እንኳ ሙሉ በሙሉ መዝጋት አይችሉም" ሲሉ ተናግረዋል።

    አሜሪካ በባሕረ ሰላጤው አገራት በኳታር፣ ባህሬን፣ ኩዌት፣ ዩኤኢ፣ ሳዑዲ አረቢያ እና ኦማን የጦር ሠፈሮች አሏት።

  8. ትራምፕ ኢራን ለሰላም ዕቅዱ የሰጠችውን ምላሽ ውድቅ አደረጉ

    ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን አሜሪካ ጦርነቱን ለማቆም ላቀረበችው ዕቅድ የሰጠችውን ምላሽ “ፈጽሞ ተቀባይነት የሌለው” ሲሉ ውድቅ አደረጉ።

    በከፊል ከኢራን መንግሥት ጋር ግንኙነት ያለው ታስኒም የቴህራን ምላሽ በአሸማጋይዋ ፓኪስታን በኩል መላኩን ዘግቧል።

    የዜና ወኪሉ የቴህራን ምላሽ ውስጥ በሁሉም ግንባሮች የሚካሄዱ ውግያዎች እንዲቆሙ፣ አሜሪካ የኢራን ወደቦች ላይ የጣለችው እገዳ እንዲነሳ፣ እንዲሁም ወደፊት ኢራን ላይ ጥቃት እንደማይፈጸም ዋስትና እንዲሰጥ ይጠይቃል።

    ከሁለት ወር በላይ በዘለቀው የኢራን ጦርነት አልፎ አልፎ የተኩስ ልውውጦች ቢኖሩም በአብዛኛው የተኩስ አቁሙ እንደቀጠለ ነው።

    ከዚህ ሳምንት ቀደም ብሎ ትራምፕ በኢራን ላይ የከፈቱት ጦርነት “በፍጥነት ይጠናቀቃል” ብለው ነበር።

    ነገር ግን የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ጦርነቱ ተጠናቅቋል ከማለታችን በፊት ኢራን ያከማቸችው የበለጸገ ዩራኒየም “መውጣት አለበት” ሲሉ ጠይቀዋል።

    ኔታንያሁ ሲቢኤስ ላይ በሚቀረበው ‘60 ሚኒትስ’ ለተሰኘ ፕሮግራም በሰጡት ቃለ ምልልስ “አሁንም ያልወደሙ የማበልጸጊያ ማዕከላት አሉ” ብለዋል።

    እሁድ ዕለት የኢራኑ ፕሬዚዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን የሰላም ዕቅዱን በቀጥታ ሳይጠቅሱ “በጠላቶቻችን ፊት አንገታችንን አንደፋም። የንግግር ወይም የድርድር ሃሳብ ሲመጣ እጅ መስጠት ወይም ማፈግፈግ ማለት አይደለም” ብለዋል።

    ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ “በተወካይ በኩል ቀረበ የተባለውን የኢራንን ምላሽ አነበብኩት፤ አልወደድኩትም። ምንም ተቀባይነት የለውም” ሲሉ ጽፈዋል።

    የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን የሆነው አክሲዮስ ውስጥ አዋቂ ምንጮችን ጠቅሶ እንደዘገበው አሜሪካ ያቀረበችው ባለ 14 ነጥብ የሰላም ዕቅድ ኢራን ኒውክሌር ማበልጸጓን እንድታቋረጥ፣ የተጣለባት ማዕቀብ እንዲነሳ እና በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የሚደረገው ነጻ እንቅስቃሴ እንዲቀጥል የሚጠይቁ ሃሳቦችን የያዘ ነው።

    መገናኛ ብዙኃኑ በዘገባው ስለ ዕቅዱ ማብራሪያ የተሰጣቸውን ሁለት በስም ያልተጠቀሱ የአሜሪካ ባለሥልጣናትን እና ሁለት ሌሎች ግለሰቦችን ጠቅሷል።

    እንዚህ ምንጮች በመግባቢያ ሰነዱ ላይ የተጠቀሱት አብዛኛዎቹ ነጥቦች ለመጨረሻው ስምምነት መነሻ በመሆን ያገለግላሉ ብለዋል።

    ኢራን የዓለም 20 በመቶ ነዳጅ እና ጋዝ የሚተላለፍበትን የባሕር ወሽመጡን እንደዘጋች ነው።

    አሜሪካ በበኩሏ ወደ ኢራን ወደቦች የሚገቡ እና የሚወጡ መርከቦችን የከለከለች ሲሆን ይህም ቴህራን ወደ ድርድር ጠረጴዛ እንድትመጣ ጫና ለመፍጠር ያለመ ነው።

    ትራምፕ እአአ ግንቦት 6 በትሩዝ ሶሻል ሚዲያ ገጻቸው ላይ ኢራን በቀረበላት የሰላም ሃሳብ የማትስማማ ከሆነ ዳግመኛ የቦምብ ድብደባው እንደሚጀመር ጽፈው “ከዚህ በፊት ከታየው ሁሉ የከፋ ይሆናል” ሲሉ አስጠንቅቀው ነበር።