ቀጥታ, የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ከኢራን ጋር የተገባው የተኩስ አቁም ስምምነት “አልፈረሰም” አሉ

የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር በሆርሙዝ ወሽመጥ ጥቃት ቢቀጥልም አገራቸው ከኢራን ጋር የገባችው የተኩስ አቁም ስምምነት “አልፈረሰም” አሉ። የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ አሜሪካ እና ኢራን ሰኞ ዕለት ጥቃት መፈጸማቸውን ቢቀጥሉም የተኩስ አቁሙ ባለበት መሆኑን ተናገሩ።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ዶናልድ ትራምፕ ኢራን መሸነፏን አምና “እጇን መስጠት አለባት” አሉ

    ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ማክሰኞ ዕለት የኢራን ጦር አቅምን አጣጥለው ቴህራን መሸነፏን አምና “እጇን መስጠት” ነበረባት ግን ያንን ለማድረግ የቴህራን ባለሥልጣናት ትምክህት ይዟቸዋል አሉ።

    ትራምፕ በኦቫል ኦቪስ ለጋዜጠኞች ሲናገሩ የኢራን ጦር ደካማ መሆኑን እና "የመጫወቻ ጠመንጃዎች" ይጠቀማሉ ሲሉ ተሳልቀዋል።

    ኢራን በአደባባይ የምትለው ሌላ ቢሆንም በምስጢር ግን ከስምምነት መድረስ ትፈልጋለች ሲሉም ተናግረዋል።

    “ጨዋታ ይጫወታሉ። ነገር ግን አንድ ነገር ልንገራችሁ፤ ከስምምነት ላይ መድረስ ይፈልጋሉ። ጦሩ ሙሉ በሙሉ ከወደመበት ማን የማይፈልግ አለ” ብለዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ “ኢራን ምንም አማራጭ የላትም” በማለት የቴህራን ባለሥልጣናት ከአሜሪካ ጋር ሲነጋገሩ እና ቴሌቪዥን ላይ ሲቀርቡ የተለያየ ነገር ይናገራሉ ሲሉ ተችዋቸዋል።

    “ምንም አማራጭ የላትም፤ ኖሯትም አያውቅም” በማለት የኢራን ጦር መሸነፉን ዳግም ተናግረዋል።

    የኢራን ጦር ባሕር ኃይል፣ አየር ኃይል ሙሉ በሙሉ መውደማቸውን የተናገሩት ፕሬዚዳንቱ “የኒውክሌር ጦር መሣሪያ እንዲኖራቸው አንፈቅድም” ሲሉ አስተየየታቸውን ሰጥተዋል።

    አሜሪካ “ኢራንን ክፉኛ ደቁሳታለች” ያሉት ትራምፕ “በጠመንጃ ብቻ ጥቂት ጀልባዎችን መቀነስ ችለናል” ብለዋል።

    ሰኞ ዕለት አሜሪካ በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የነበሩ የኢራን ጀልባዎችን መምታቷን አስታውቃለች።

    ወሳኙ የባሕር መተላለፊያ በኢራን በመዘጋቱ መውጫ አጥተው የቆዩ መርከቦችን እንደሚያስወጡ የተናገሩት ትራምፕ፤ “ሰባት ትንሽ ጀልባዎችም ወይም እነሱ ‘ፈጣን’ ጀልባ የሚሏቸውን መትተናል። የቀሯቸው እነሱ ብቻ ነበሩ” ብለዋል።

    ትራምፕ በኦቫል ኢፊስ በሰጡት መግለጫ ኢራን በጦርነቱ መጀመርያ ወቅት 159 መርከቦች እንደነበሯት ገልጸው “ያሏቸው እያንዳንዱ መርከብ ከባሕር ወለል በታች ነው የሚገኙት’ ሲሉ ተናግረዋል።

    በባሕር ኃይላቸው ምንም ዓይነት መርከብ የላቸውም ያሉት ትራምፕ ከዚያ ይልቅ ስምንት “ትንሽ ጀልባዎች” ነበሩ እነርሱም “ሁሉም ወድመዋል” ብለዋል።

    አክለውም “ከእኛ ታላቅ ባሕር ኃይል ጋር ለመገዳደር ትንንሽ ጀልባ እየፈለጉ ነው” ሲሉ ተናግረዋል።

    ኢራን የተኩስ አቁሙን ጣሰች የሚባለው ምን ስታደርግ ነው ተብለው የተጠየቁት ትራምፕ “ስለምነግራችሁ ታውቁታላችሁ” በማለት መልሰዋል።

    “በጣም አስፈላጊው ነገር ምን ማድረግ እንዳለባቸው እና እንደሌለባቸው ያውቃሉ” ብለዋል።

    ኢራን መሸነፏን አምና “እጇን መስጠት አለባት” ያሉት ትራምፕ “ይህ መደበኛ ውጊያ ቢሆን ኖሮ ይሄኔ አቁመውት ነበር” ብለዋል።

    አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች የሚንቀሳቀሱ መርከቦች ማገዷን በተመለከተም ሲናገሩ አንድም መርከብ ማለፍ እንዳልቻለ አብራርተዋል።

    አንድ መርከብ ለማለፍ ሲሞክር ማስጠንቀቂያ ከተሰጠው በኋላ የአሜሪካ ጦር “በአንድ ተኩስ ሞተሩን መትቶታል” ብለዋል።

    ትራምፕ የሆርሙዝ ወሽመጥን ለማስከፈት ከጃፓን እና ደቡብ ኮሪያ ጋር “ትልልቅ ስምምነቶችን” እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል።

    በሚቀጥለው ሳምንት ወደ ቻይና በሚጓዙበት ወቅት ከፕሬዚዳንት ዢ ጂንፒንግ ጋርም መልካም ንግግር ይኖራል ብለው እንደሚጠብቁ ተናግረዋል።

    ትራምፕ አሜሪካ በኢራን ወደቦች ላይ ጣለችው እገዳ እየሰራ መሆኑን ገልጸው ቴህራን “ስምምነት ላይ መድረስ ትፈልጋለች” ብለዋል።

    “ጨዋታ ይጫወታሉ። የምነግራችሁ ነገር ግን ከስምምነት መድረስ ይፈልጋሉ” ብለዋል።

  2. የሆርሙዝ ወሽመጥ ለእንቅስቃሴ ክፍት መሆኑን አሜሪካ አስታወቀች

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት እና የአሜሪካ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ ጄኔራል ዳን ኬን በጋራ በመሆን ዛሬ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ የሆርሙዝ ወሽመጥ ክፍት መሆኑን ተናገሩ።

    የመከላከያ ሚኒስትሩ አሜሪካ “ጦርነት አትፈልግም” ያሉ ሲሆን ነገርግን ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን ዘግታ እንድትቀመጥ እንደማይፈቅዱ ተናግረዋል።

    ሚኒስትሩ አክለውም የ’ፕሮጀክት ፍሪደም’ ግብ “ገለልተኛ የሆኑ የንግድ መርከቦችን ከኢራን ጥቃት መከላከል” መሆኑን ተናግረዋል።

    ሄግሴት አክለውም ሁለት የአሜሪካን ባንዲራ የሚያውለበልቡ መርከቦች በወሽመጡ በኩል ማለፋቸውን ገልጸው “መስመሩ ነጻ ነው” በማለት ኢራናውያን “ተዋርደዋል” ሲሉ አስታውቀዋል።

    የተኩስ አቁሙ “አልፈረሰም” ያሉት ሄግሴት ኢራን ዳግም ግጭቱን ላለመጀመር “እንድትጠነቀቅ” አሳስበዋል።

    የአሜሪካ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ ጄኔራል ዳን ኬን በበኩላቸው ኢራን የተኩስ አቁሙ ከተጀመረ አንስቶ አስር ጊዜ ያህል የአሜሪካ ጦር ላይ ጥቃት ፈጽማለች ሲሉ ከስሰዋል።

    አክለውም እነዚህ ጥቃቶች “በአሁን ሰዓት” ጦርነቱን ለመጀመር “ከመስፈርቱ በታች” ናቸው ብለዋል።

    ኬን ኢራንን በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ያለውን የዓለም አቀፉን የአቅርቦት ሰንሰለት "እንደ ጦር መሣሪያ በመጠቀም” የወነጀሏት ሲሆን የመላው ዓለም ምጣኔ ሃብትን "አግታ ለመያዝ ጥረት አድርጋለች” ብለዋል።

    22,500 ባህረተኞች እና 1,550 የንግድ መርከቦች በባሕረ ሰላጤው መንቀሳቀሰሻ አጥተው መቆማቸውንም ጄነራሉ በመግለጫቸው ላይ ተናገረዋል።

  3. የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ከኢራን ጋር የተገባው የተኩስ አቁም ስምምነት “አልፈረሰም” አሉ

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር በሆርሙዝ ወሽመጥ ጥቃት ቢቀጥልም አገራቸው ከኢራን ጋር የገባችው የተኩስ አቁም ስምምነት “አልፈረሰም” አሉ።

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት ዛሬ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ አሜሪካ እና ኢራን ሰኞ ዕለት ጥቃት መፈጸማቸውን ቢቀጥሉም የተኩስ አቁሙ ባለበት መሆኑን ተናግረዋል።

    የተኩስ አቁሙ “አልፈረሰም” ያሉት የመከላከያ ሚኒስትሩ አሜሪካ ሰኞ ዕለት በወሽመጡ የጀመረችውን ዘመቻ “የተለየ፣ የተናጠል ፕሮጀክት ነው” ብለዋል።

    ኢራን ዳግም ግጭቱን ላለመጀመር “እንድትጠነቀቅ” አሳስበው “አሁን የተኩስ አቁሙ ባለበት” መሆኑን ተናግረዋል።

    የአሜሪካ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ ጄኔራል ዳን ኬን በበኩላቸው ኢራን ዘጠኝ ጊዜ የንግድ መርከቦች ላይ መተኮሷን ተናግረዋል።

    ቴህራን ሁለት የጭነት መርከቦችን መቆጣጠሯን የገለጹት ጄነራሉ፣ የተኩስ አቁም ስምምነቱ ከተጀመረ ጀምሮ 10 ጊዜ የአሜሪካ ጦር ላይ ጥቃት ፈጽማለች ሲሉ ወንጅለዋታል።

    ጠቅላይ አዛዥ ጄኔራል ዳን ኬን ኢራን ላይ ሙሉ በሙሉ ጥቃት ለመጀመር አሁን ጊዜው አይደለም ያሉት ሲሆን፣ የቴህራን ሚሳዔሎች፣ ድሮኖች እና አነስተኛ ጀልባዎች በትናንትናው ዕለት በአሜሪካ ጦር ላይ የፈጸሙት ጥቃትን መመከታቸውን ተናግረዋል።

    22,500 ባህረተኞች እና 1,550 የንግድ መርከቦች በባሕረ ሰላጤው መንቀሳቀሰሻ አጥተው መቆማቸውንም ጨምረው ገልጸዋል።

  4. በኢራን ጥቃት የተፈጸመበት የኤምሬትስ የነዳጅ ማዕከል ምን ያህል ወሳኝ ነው?

    ኢራን በመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ላይ ስትፈጽም ለቆየችው ጥቃት ዋነኛ ዒላማ የሆነችው የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ፉጃይራህ የተባለው ዋነኛው የነዳጅ ማምረቻ ኢንዱስትሪ ዞን በቴህራን መመታቱን አስታውቃለች።

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ላለፉት ሳምንታት የተኩስ አቁም ከተደረሰ በኋላ የተፈጸመውን ጥቃት አደራዳሪዋ ፓኪስታንን ጨምሮ በርካታ አገራት እና የአረብ ሊግ አውግዘውታል።

    ከዚህ ቀደምም ጥቃት የተፈጸመበት ፉጃይራህ የተባለው የነዳጅ ምርት ማዕከል የጥቃት ዒላማ እንዲሆን ያደረገው ምክንያት ምንድን ነው? ስለዞኑ ምን የሚታወቅ ነገር አለ?

    ፉጃይራህ የነዳጅ ኢንዱስትሪ ዞን በኤምሬትስ ምሥራቃዊ የባሕር ዳርቻ ከወሳኙ የባሕር መተላለፊያ ሆርሙዝ በስተደቡብ ይገኛል። ዞኑ ከሕንድ ውቅያኖስ ጋር በቀጥታ የሚገናኝ ቦታ ላይ ያለ ነው።

    ፉጃይራህ በመካከለኛው ምሥራቅ ከሚገኙ ግዙፍ የነዳጅ ማከማቻ ማዕከላት መካከል አንዱ ነው። በዚህም ወደ 70 ሚሊዮን በርሜል የሚደርስ ነዳጅ ማከማቸት የሚችል አቅም አለው።

    የማከማቻው ነዳጅ የመያዝ አቅም በአጠቃላይ በዓለም ዙሪያ በአንድ ቀን ውስጥ ጥቅም ላይ ከሚውለው ነዳጅ ውስጥ ሦስት አራተኛውን ያህል ያከማቻል።

    ይህም ማለት ዓለማችን በቀን 100 ሚሊዮን በርሜል በላይ የምትጠቀም ሲሆን፣ ፉጃይራህ ላይ የሚከማቸው ደግሞ 70 ሚሊዮን በርሜል የሚሆን ነው።

    ምንም እንኳን በጦርነቱ የተነሳ የሆርሙዝ ወሽመጥ ቢዘጋም ከአቡ ዳቢ የነዳጅ ማውጫዎች ከሚነሳው ደፍድፍ ነዳጅ የተወሰነው በቧንቧ አማካይነት በፉጃይራህ በኩል በመርከቦች በኩል ወደ ዓለም ገበያ እየቀረበ ይገኛል።

  5. እስራኤል በሊባኖስ 17 ሰዎችን በገደለች ማግሥት ነዋሪዎች ለቅቀው እንዲወጡ ትዕዛዝ አወጣች

    የሊባኖስ ተኩስ አቁም ከተጀመረ ወዲህ ከፍተኛ ሞት ከታየባቸው ቀናት አንዱ በሆኖ በተመዘገበው በትናንትናው ዕለት እስራኤል በፈጸመችው ጥቃት 17 ሰዎች መገደላቸውን የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር አስታወቀ።

    ካለፈው ሳምንት ማክሰኞ አንስቶ በተፈጸሙ ጥቃቶች የተገደሉ ሰዎች ብዛት 110 መድረሱን የሊባኖሱ ጤና ሚኒስቴር ገልጿል።

    ሚኒስቴሩ ቁጥር ንጹኃን እና ተዋጊዎችን ለይቶ አላስቀመጠም። ይሁን እንጂ ከተገደሉት ሰዎች መካከል ሁለት ሕጻናት ሲሆኑ፣ 14 ሕጻናትም ተጎድተዋል።

    ጥቃት የምትፈጽመው በሺዓ እስላማዊው ቡድን ሄዝቦላህ ላይ መሆኑን የምትናገረው እስራኤል በበኩሏ፤ በደቡባዊ ሊባኖስ ሁለት ከተሞች የሚገኙ ነዋሪዎች ለቅቀው እንዲወጡ ትዕዛዝ አስተላልፋለች።

    የእስራኤል ጦር “ሄዝቦላህ በሚፈጽመው የተኩስ አቁም ስምምነት ጥሰት” ምክንያት በቡድኑ ላይ “በኃይል ለመንቀሳቀስ መገደዱን” ገልጿል።

    የእስራኤል ጦር ይህንን ትዕዛዝ ከማስተላለፉ አስቀድሞ በኢራን የሚደገፈው ሄዝቦላህ በደቡባዊ ሊባኖስ የሚገኙ የእስራኤል ወታደሮች ላይ ጥቃት ፈጽሟል የሚል ክስ አሰምቶ ነበር። ሄዝቦላህ ስለ ክሱ አስተያየት አልሰጠም።

    ባለፈው አንድ ሳምንት ውስጥ 17 ወታደሮች እንደተገደሉባት የምትናገረው እስራኤል፤ ሄዝቦላህ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሮኬቶች እና ድሮኖችን እንዳስወነጨፈ በመጥቀስ ትከስሳለች።

    ሄዝቦላህ፤ እስራኤል እና ሊባኖስ የደረሱበት የተኩስ አቁም ስምምነት ፈራሚ አካል አይደለም።እስራኤል ለስምምነቱ የምትገዛ ከሆነ ግን ተኩስ አቁሙን እንደሚቀበል ጠቆሞ ነበር።

    የእስራኤል ጦር በስምምነቱ መሠረት “የታቀዱ፣ አይቀሬ ወይም ቀጣይ ጥቃቶችን” መፈጸም እንደተፈቀደለት ይናገራል። የሊባኖስ ባለሥልጣናት ስምምነቱ በዚህ መልኩ መተርጎሙን የሚቃወሙ ሲሆን፣ እስራኤል በተደጋጋሚ የተኩስ አቁሙን ጥሳለች የሚል ክስ ያቀርባሉ።

  6. ዓለም አቀፉ የነዳጅ ጫኝ መርከብ ባለቤቶች ማኅበር የአሜሪካ እጀባ ዕቅድ “ከፍተኛ ለውጥ አያመጣም” አለ

    ዓለም አቀፉ የገለልተኛ ነዳጅ ጫኝ መርከብ ባለቤቶች ማኅበር ‘ኢንተርታንኮ’፤ አሜሪካ ይፋ ያደረገችው የንግድ መርከቦችን አጅቦ በሆርሙዝ ወሽመጥ የማሳለፍ ዕቅድ "በከፍተኛ ሁኔታ የሚለውጠው ነገር የለም” አለ።

    ‘ሜርስክ’ የተሰኘው ግዙፍ የሎጂስቲክ ኩባንያ አንድ መርከቡ በአሜሪካ ጦር ታጅቦ ሰኞ ዕለት በሆርሙዝ ወሽመጥ ማለፉን አስታውቋል። ከቢቢሲ ‘ቱዴይ’ ፕሮግራም ጋር ቆይታ ያደረጉት የኢንተርታንኮ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ቲም ዊልኪንስ፤ የመርከቡ ማለፍ እገዳውን በማቃለል ረገድ ያለው ተጽዕኖ “ውቅያኖስ ውስጥ እንዳለ ጠብታ ነው” ብለዋል።

    ዊልኪንስ “በጣም ጠባብ በሆነ ሁኔታ ውስጥ በቅርብ እጀባ ተደርጎለት ያለፈው አንድ መርከብ ነው” ብለዋል። የመርከቡ ማለፍ መውጫ ላጡት የተቀሩት መርከቦች “ምንም ነገር ላይ ከፍተኛ ለውጥ አያመጣም” ሲሉ ተናግረዋል።

    ገለልተኛ የነዳጅ ጫኝ ባለቤቶችን የሚወክለውን ማኅበር የሚመሩት ማኔጂንግ ዳይሬክተር አክለውም፤ “ተግባራዊ እየሆነ ያለ ቅርጽ ያለው ወይም የተቀናጀ ሥርዓት የለም። ስለዚህ አባላቶቻችን እየጠየቁ ያሉት መሠረታዊ ጥያቄዎችን ነው፤ እነዚህን ጉዞዎች የሚያስጀምረው ማነው?” ብለዋል።

    “መርከቦቹን ወክሎ ከባለሥልጣናቱ ጋር የሚነጋገረው ማነው? ወሳኙ ጉዳይ ደግሞ በጉዞው ወቅት መርከቦቹ ከኢራን ኃይሎች ችግር ቢያጋጥማቸው የተያዘው ዕቅድ ምንድነው?” ሲሉም ጠይቀዋል።

  7. ትራምፕ ኢራን የአሜሪካ መርከቦችን ካጠቃች "ከምድረ ገጽ ትጠፋለች" ሲሉ ዛቱ

    ኢራን እንደዛተችው በአሜሪካ መርከቦች ላይ ጥቃት ከፈጸመች ‘ከምድረ ገጽ ትጠፋለች’ ሲሉ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስጠነቀቁ።

    ትራምፕ ከፎክስ ኒውስ ቴሌቪዥን ጋር ሰኞ ዕለት ባደረጉት ቃለ ምልልስ፤ አሜሪካ ‘ፕሮጀክት ፍሪደም’ በሚል በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚተላለፉ መርከቦችን ለመጠበቅ በምትወስደው እርምጃ ወቅት በመርከቦቿ ላይ ጥቃት ከተፈጸመ “ኢራን ከምድረ ገጽ ትጠፋለች” ሲሉ ዝተዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ጨምረውም በድርድሩ ሂደት ኢራን “የበለጠ ልፍስፍስ” እየሆነች እንደሆነ እና የአገራቸው ሠራዊትም ከኢራን የተሻለ ወታደራዊ አቅም እንዳለው ተናግረዋል።

    ይህ የትራምፕ ቃለ ምልልስ የተሰማው የአሜሪካ ኃይሎች የሆርሙዝ ወሽመጥን ለማስከፈት እየወሰዱት ባለው እርምጃ ሰባት የኢራን “ትንንሽ ጀልባዎችን” መምታታቸውን በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ካስታወቁ በኋላ ነው።

    በተጨማሪም አሜሪካ የኢራንን ድሮኖች እና ሚሳዔሎችን መትታ መጣሏን አስታውቃለች።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ በጦርነቱ ምክንያት በሆርሙዝ ወሽመጥ መተላለፍ ላልቻሉት የንግድ መርከቦቻቸው መንገድ መንገድ እንዲያስከፍቱ “በዓለም ዙሪያ ካሉ አገራት” ቀረበልኝ ባሉት ጥያቄ መሠረት ‘ፕሮጀክት ፍሪደም’ የተባለ ዘመቻ ከሰኞ ጀምሮ እያካሄዱ ነው።

    በዚህም የአሜሪካ ኃይሎች የመርከቦቹን ደኅንነት ለመጠበቅ ሆርሙዝ ላይ በመሰማራት ጥቃት እንዳይደርስባቸው ጥበቃ እንደሚያደርጉ ተገልጿል። ነገር ግን ኢራን ይህንን የአሜሪካ እርምጃ በመቃወም የአሜሪካ ባሕር ኃይል መርከቦችን እንደምትመታ እየዛተች ነው።

  8. አሜሪካ የተኩስ አቁም ስምምነቱን ጥሳለች ሲሉ የኢራን ከፍተኛ ተደራዳሪ ገለጹ

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ አሜሪካ በሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ ላይ ያለውን የመርከብ እንቅስቃሴ እና የኢነርጂ ደኅንነት አደጋ ላይ ጥላለች ሲሉ ገለጹ።

    ባለፈው ወር ከአሜሪካ ጋር በተደረገው ንግግር ወቅት ከፍተኛ ተደራዳሪ የነበሩት የአሜሪካ አፈ ጉባዔው መሐመድ ባጊር ጋሊባፍ ዛሬ ጠዋት በኤክስ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሁፍ አሜሪካን "የተኩስ አቁም ስምምነቱን በመጣስ" እና በባሕር ወሽመጡ ላይ "እገዳ" በመጣል ከሰዋል።

    ይህንን ያሉት ዶናልድ ትራምፕን "የነፃነት ፕሮጀክት" ሰኞ ዕለት መጀመሩን ከገለጹ በኋላ ነው። "አሁን ያለው ሁኔታ አይቀጥልም” ያሉ ሲሆን፣ ኢራን "እስካሁን አልጀመረችም" በማለት አፈ ጉባኤው ጽሁፋቸውን ደምድመዋል።

  9. በኢራን የኒውክሌር ፕሮግራም ላይ የደረሰው አዲስ ጉዳት ውስን እንደሆነ የአሜሪካ የስለላ መረጃ አመለከተ

    ሁለት ወር ባለፈው ጦርነት የኢራን የኒውክሌር ፕሮግራም ላይ የደረሰው አዲስ ጉዳት ውስን በመሆኑ ቴህራን የኒውክሌር የጦር መሣሪያ ለመገንባት የሚያስፈልጋት ጊዜ ከአንድ ዓመት ያልበለጠ መሆኑን የአሜሪካ የስለላ መረጃ ማሳየቱን ሮይተርስ ዘገበ።

    ዜና ወኪሉ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸውን ሦስት ምንጮች ጠቅሶ ያወጣው ዘገባ እንደሚያመለክተው፤ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን የኒውክሌር ቦንብ እንዳትሠራ ለማስቆም ሲሉ የካቲት ላይ የከፈቱት ጦርነት በቴህራን የኒውክሌር ፕሮግራም ላይ ያንን ያህል ለውጥ አላመጣም።

    አሜሪካ እና እስራኤል ጦርነቱን የጀመሩት መደበኛ ወታደራዊ ዒላማዎችን በማጥቃት ቢሆንም ኋላ ላይ እስራኤል በርከት ያሉ ወሳኝ የኒውክሌር ተቋማትን መትታለች።

    ይሁን እንጂ እነዚህ ጥቃቶች የኢራን የኒውክሌር መሣሪያ ትታጠቅበታለች ተብሎ የሚታሰበው የጊዜ ሰሌዳ ላይ ጉልህ ለውጥ ባለማምጣታቸው፤ የቴህራንን የኒውክሌር ፕሮግራም ማውደም ወይም ያላትን የበለጸገ ዩራኒየም ክምችት ማስወጣት በአማራጭነት ተቀምጠዋል።

    እስራኤል እና አሜሪካ ባለፈው ዓመት ሰኔ ላይ ናታንዝ፣ ፎርዶው እና ኢስፋሃን የኒውክሌር ተቋማት ላይ ጥቃት ፈጽመው ነበር። ሮይተርስ የጠቀሰው የአሜሪካ የስለላ መረጃ እንደሚያሳየው እነዚህ ጥቃቶች ኢራንን የኒውክሌር መሣሪያ ለመታጠቅ የሚያስፈልጋት ጊዜ የገፉት ከዘጠኝ ወር እስከ አንድ ዓመት ለሚደርስ ጊዜ ብቻ ነው።

    በባለፈው ዓመት ጥቃት ሥራ ላይ የነበሩት ሦስት የማበልጸጊያ ተቋማት ቢመቱም፤ የተባበሩት መንግሥታት የኒውክሌር ተቆጣጣሪ ተቋም 440 ኪሎ ግራም የሚደርሰው የኢራን 60 በመቶ የበለጸገ ዩራኒየም የት እንደሚገኝ ማረጋገጥ አልቻለም።

    ግማሽ ያህሉ በኢስፋሃን የኒውክሌር ምርምር ተቋም የምድር ስር ይገኛል ተብሎ እንደሚታመን ዜና ወኪሉ ጠቅሷል።

    የአሜሪካ እና ኢራን ባካሄዱት ድርድር ስምምነት ላይ እንዳይደርሱ ካደረጓቸው ጉዳዮች ዋነኛው የቴህራን የኒውክሌር ፕሮግራም ነው። ፕሬዝዳንት ትራምፕ ኢራን የኒውክሌር መሣሪያ እንድትታጠቅ እንደማይፈቅዱ ተናግረዋል።

    የኒውክሌር ፕሮግራሟ ለሰላማዊ ዓላማ የሚውል እንደሆነ የምትገልጸው ኢራን በበኩሏ ዩራኒየም የማበልጸግ መብቷ እውቅና እንዲሰጠው የሚጠይቅ የስምምነት ሃሳብ ማቅረቧ ተዘግቧል።

  10. አሜሪካ በሰባት የኢራን ፈጣን ጀልባዎች ላይ ጥቃት መፈጸሟን አስታወቀች

    አሜሪካ በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የነበሩ ሰባት የኢራን “ፈጣን ጀልባዎች” ላይ ጥቃት መፈጸሟን ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ተናገሩ።

    ወሳኙ የባሕር መተላለፊያ በኢራን በመዘጋቱ መውጫ አጥተው የቆዩ መርከቦችን እንደሚያስወጡ የተናገሩት ትራምፕ፤ “ሰባት ትንሽ ጀልባዎችም ወይም እነሱ ‘ፈጣን’ ጀልባ የሚሏቸውን መትተናል። የቀሯቸው እነሱ ብቻ ነበሩ” ብለዋል። የአሜሪካ ጦር እንደገለጸው ጀልባዎቹ ላይ ጥቃት የተፈጸመው ሄሊኮፕተሮችን በመጠቀም ነው።

    የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዛ (ሴንትኮም) ባወጣው መግለጫ “ዛሬ የንግድ መርከቦች ላይ አደጋ የጣሉትን የኢራንን አነስተኛ ጀልባዎች ለማስወገድ ሲ ሃውክ እና የአሜሪካ ጦር ኤኤች-64 አፓች ሄሊኮፕተሮች ጥቅም ላይ ውለዋል” ብሏል።

    ፕሬዝዳንቱ ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ ኢራን የደቡብ ኮሪያ መርከብን ጨምሮ ከግጭቱ ጋር “ግንኙነት በሌላቸው አገራት ላይ ተኩሳለች” ሲሉ ከስሰዋል።

    የደቡብ ኮሪያ መንግሥት ትናንት እንዳስታወቀም ‘ኤችኤምኤም ናሙ’ የተሰኘ የአገሪቱ የጭነት መርከብ ሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ “ጥቃት እንደሆነ በተጠረጠረ” ክስተት ጉዳት ደርሶበታል። የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች አቅራቢያ ቆሞ የነበረው ይህ መርከብ 24 ሠራተኞችን ይዞ እንደነበር የአገሪቱ መንግሥት ገልጿል። በሰዎች ላይ የደረሰ ጉዳት ስለመኖሩ አልተነገረም።

    ይህንን ጉዳይ የጠቀሱት ፕሬዝዳንት ትራምፕ “ምናልባት ደቡብ ኮሪያ የምትመጣበት እና ተልዕኮውን የምትቀላቀልበት ጊዜ አሁን ነው” ብለዋል።

    የኢራን መገናኛ ብዙኃን ግን የትራምፕ ተፈጽሟን ያሉትን የጀልባዎች ጥቃት አስተባብለዋል። አንድ ወታደራዊ ምንጭን የጠቀሰው ኢራኑ ታስኒም ዜና ወኪል እንደዘገባው ከሆነ ጥቃት የደረሰባቸው ሁለት የጭነት መርከቦች ናቸው። በዚህም አምስት ንጹኃን ተገድለዋል ብሏል።

    ጥቃት ተፈጽሟል ከመባሉ አስቀድሞ የአሜሪካ ባሕር ኃይል አውዳሚ መርከብ እና ሁለት የአሜሪካን ባንዲራ የሚያውለበልቡ የንግድ መርከቦች በወሽመጡ ማለፋቸውን ዋሽንግተን አስታውቃ ነበር።

    ይህንን ገለጻ “ሙሉ በሙሉ ሐሰተኛ” ስትል የጠራቸውን ኢራን በበኩሏ የአሜሪካ የጦር መርከብ ላይ የማስጠንቀቂያ ተኩስ መተኮሷን ገልጻለች፤ የአሜሪካ ጦር ይህንን አስተባብሏል።

    ይሁን እንጂ ሰኞ ዕለት ‘መርስክ’ የተሰኘው የመርከብ ኩባንያ እንደገለጸው የአሜሪካ ሰንደቅ ዓላማ ያነገቡ እና ጦርነቱ ከተጀመረበት የካቲት አንስቶ በባሕረ ሰላጤው ቆመው የነበሩ መርከቦቹ በወሽመጡ ማለፋቸውን አስታውቋል።

    ኩባንያው “በአሜሪካ ወታደራዊ ጥበቃ ስር ሆኖ መርከብ የማስወጣት ዕድል እንደቀረበለት” ገልጿል። “ይህንን ተከትሎም መርከቡ በአሜሪካ ጦር ታጅቦ ከፋርስ ባሕረ ሰላጤ ወጥቷል” ብሏል።

  11. የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የነዳጅ ኢንዱስትሪ ዞን የድሮን ጥቃት ተፈጸመበት

    የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ቁልፍ የነዳጅ ወደብ በሆነው ፉጃኢራህ ላይ በተፈጸመ የድሮን ጥቃት ሦስት ሰዎች “መጠነኛ ጉዳት” እንደደረሰባቸው የአካባቢው ባለሥልጣናት ተናገሩ።

    የኢምሬቶች ትልቁ ወደብ እና የነዳጅ ማከማቻ ስፍራ የሆነው ፉጃኢራህ፤ በኢራን ድሮን ጥቃት ከተፈጸመበት በኋላ ከፍተኛ እሳት መከሰቱን ተገልጿል።

    በደረሰው ጥቃት የተጎዱት የሕንድ ዜግነት ያላቸው ሦስት ሰዎች ወደ ሆስፒታል ተወስደዋል ተብሏል። የከተማው የመገናኛ ብዙኃን ቢሮ ያወጣው መግለጫ እንደሚያሳየው የደረሰው ጉዳት “መጠነኛ” የሚባል ነው።

    ፉጃኢራህ የነዳጅ ኢንዱስትሪ ዞን መካከለኛው ምሥራቅ ውስጥ ከሚገኙ ግዙፍ የነዳጅ ማከማቻዎች አንዱ ነው። የተኩስ አቁም ስምምነት ከመደረሱ በፊትም በኢራን ጥቃት ተፈጽሞበት ነበር።

    ስፍራው መመታቱ የተሰማው፤ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች መከላከያ ሚኒስትር ከኢራን የተወነጨፉ ሦስት ሚሳዔሎችን ማክሸፉን ከገለጸ በኋላ ነው። አራተኛው ሚሳዔል ባሕር ላይ እንደወደቀ ተገልጿል።

    እስካሁን ድረስ ኢራን ስለ ጥቃቱ አስተያየት አልሰጠችም።

  12. ኢራን መርከቦች በሆርሙዝ በኩል አልፈዋል የሚለው የአሜሪካ ገለጻ “ሙሉ በሙሉ ሐሰት ነው” አለች

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ፤ የአሜሪካ ጦር በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል መርከቦች ስለማለፋቸው የሰጠው ገለጻ “ፍጹም ውሸት” ነው ሲል አጣጣለ።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ፤ ሁለት የአሜሪካ ሰንደቅ ዓላማን የሚያውለበልቡ የንግድ መርከቦች “በተሳካ ሁኔታ በሆርሙዝ ወሽመጥ ማለፋቸውን” ገልጾ ነበር።

    በኢራን መገናኛ ብዙኃን የወጣው የአብዮታዊ ዘቡ መግለጫ ግን “በቅርብ ሰዓታት አንድም የንግድ ወይም ነዳጅ ጫኝ መርከብ” በሆርሙዝ ወሽመጥ አላለፈም ብሏል።

    የአሜሪካን መግለጫ “መሠረተ ቢስ እና ሙሉ በሙሉ ሐሰት” ሲል የጠራው የኢራን አብዮታዊ ዘብ፤ ከባሕር ኃይሉ ትዕዛዝ ውጪ የሚደረግ ማንኛውም እንቅስቃሴ “ከፍተኛ አደጋ እንደሚገጥመው” አስጠንቅቋል።

    ቢቢሲ ቬሪፋይ የአሜሪካን ገለጻ እውነተኛነት ለማረጋገጥ ጥረት እያደረገ ነው። የባሕር ጉዞ መከታተያ የሆነው ‘ማሪን ትራፊክ’ ድረ ገጽ ከአሜሪካ ገለጻ ጋር ተመሳሳይ የሆነ የመርከብ ጉዞ መደረጉን አያሳይም።

    ይሁን እንጂ መርከቦች አቅጣጫ ጠቋሚያቸውን አጥፍተው ጉዞ ሊያደርጉ ስለሚችል ትክክለኛ ቦታቸው ሳይገለጽ አልፈው ሊሆን የሚችልበት ዕድል አለ።

  13. የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ከኢራን ሚሳዔል እንደተተኮሰባት አስታወቀች

    የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች መከላከያ ሚኒስቴር ከኢራን የተወነጨፉ ሦስት ሚሳዔሎችን ማክሸፉን እና አራተኛው ባሕር ላይ መውደቁን አስታወቀ።

    መከላከያ ሚኒስትሩ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጹ እንዳሰፈረው፤ በአገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች ፍንዳታ የተሰማው በከሸፉት ሚሳዔሎች ምክንያት ነው።

    ሚኒስቴሩ ይህንን ያለው፤ የአገሪቱ የአደጋ ጊዜ አስተዳደር ባለሥልጣን ለተወነጨፉ ሚሳዔሎች ምላሽ እየተሰጠ መሆኑን ካስታወቀ በኋላ ነው። ባለሥልጣኑ፤ የአገሪቱ ዜጎች ደኅንነቱ የተጠበቀ ስፍራ ውስጥ እንዲቆዩ አሳስቦ ነበር።

    እስካሁን ኢራን ስለ ጥቃቱ አስተያየት አልሰጠችም። በአሜሪካ እና እስራኤል ጦርነት የተከፈተባት ኢራን፤ ኤምሬቶችን ጨምሮ የባሕረ ሰላጤው አገራትን በማጥቃት አጸፋ ስትሰጥ ቆይታለች።

    ከአሜሪካ ጋር ከተደረሰው የተኩስ አቁም ስምምነት በኋላ ግን ጥቃቶቹ ረግበው ነበር። አሁን ኤምሬቶች ላይ ጥቃት የተፈጸመው አሜሪካ በኢራን በተዘጋው ሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚጓዙ መርከቦችን እንደምታጅብ ካስታወቀች በኋላ ነው።

  14. አሜሪካ በኢራን ኃይሎች እና የሚሳዔል ይዞታዎች ላይ እርምጃ ልትወስድ መሆኑ ተነገረ

    በባሕረ ሰላጤው አካባቢ የተሰማሩት የአሜሪካ ኃይሎች በኢራን ሠራዊት እና ይዞታዎች ላይ እርምጃ እንዲወስዱ መመሪያ እንደተላለፈላቸው ተዘገበ።

    የአሜሪካ የዜና ድረ ገጽ የሆነው አክሲዮስ አንድ የአገሪቱን ከፍተኛ ባለሥልጣን ጠቅሶ እንደዘገበው በቀጣናው ያሉ የአሜሪካ ኃይሎች በሚወስዱት እርምጃ ዙሪያ የነበረው መመሪያ ተለውጧል።

    ስማቸው ያልተጠቀሰው ባለሥልጣን ተናገሩት እንደተባለው በባሕረ ሰላጤው የተሰማሩት የአሜሪካ ኃይሎች “የኢራንን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ፈጣን ጀልባዎች ወይም የሚሳዔል ማስወንጨፊያ ቦታዎችን” ዒላማ እንዲያደርጉ ፈቃድ ተሰጥቷቸዋል።

    የአሜሪካ ሠራዊት ይህንን እርምጃ እንዲወስድ የታዘዘው በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል በሚያልፉ መርከቦች ላይ ተጨባጭ ስጋት ይፈጽማሉ ብለው ባመኗቸው ዒላማዎች ላይ ነው።

    የአሜሪካ ሠራዊት እርምጃ የሚወስድባቸው ዒላማዎችን በተመለከተ አዲስ መመሪያ የወጣው አሜሪካ በሆርሙዝ በኩል ለሚተላለፉ መርከቦችን ከለላ እንደምትሰጥ ካሳወቀች በኋላ ነው።

    በዚህም ሳቢያ በኢራን እና በአሜሪካ መካከል ያለው ውጥረት እየተባባሰ ሲሆን፣ ኢራን በአሜሪካ የጦር መርከቦች ላይ የሚሳዔል ጥቃት መፈጸሟን ስታስታውቅ አሜሪካ ደግሞ ዜናውን በማስተባበል መርከቦቿ በፋርስ ባሕረ ሰላጤ ላይ እየተንቀሳቀሱ መሆናቸውን ገልጻለች።

  15. በሆርሙዝ የሚያልፉ መርከቦችን ማጀብ አደጋ እንዳለው የቀድሞ የአሜሪካ ባሕር ኃይል ካፒቴን ተናገሩ

    በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚጓዙ መርከቦችን ለማጀብ የሚዘጋጅ ማንኛውም ዕቅድ “ከፍተኛ አደጋ” እንደሚያስከትል የቀድሞ የአሜሪካ ባሕር ኃይል ካፒቴን ለቢቢሲ ተናገሩ።

    የሦስት የአሜሪካ ጦር መርከቦች አዛዥ የነበሩት ኬቪን ኤየር እንዳስረዱት፤ ዋሽንግተን ልትተገበር ያቀደችው መርከቦችን “ለመምራት እና ለማቀናጀት ወይስ በቀጥታ ወደ ውስጥ ገብቶ የተለመደውን የእጀባ” ተግባር ማስፈጸም የሚለው ግልጽ አይደለም።

    “በእነዚህ ሁለት ነገሮች መካከል ያለው ልዩነት በምሽት እና በቀን መካከል እንዳለው ልዩነት ነው። በቀጥታ እጀባ ማድረግ እጅግ አደገኛ እና አስቸጋሪ መፍትሔ ነው” ብለዋል።

    ኢራን አሁንም በርካታ ፀረ መርከብ ባለስቲክ ሚሳዔሎች፣ 1,000 የሚደርሱ ፀረ መርከብ ድሮኖች እና “ሮኬት ሊታጠቁ የሚችሉ በመቶዎች የሚቆጠሩ ፈጣን የቅኝት ጀልባዎች” እንዳሏት አንስተዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ በሆርሙዝ በኩል ማለፍ ያልቻሉ መርከቦችን እንደሚያስወጡ ከተናገሩ በኋላ የአሜሪካ ባሕር ኃይል አውዳሚ መርከቦች እና የአሜሪካ ሰንደቅ ዓላማን ያነገቡ የንግድ መርከቦች ማለፋቸው ተገልጿል።

    ይህ ከመሰማቱ አስቀድሞ የኢራን ጦር የአሜሪካ መርከቦች ወደ ወሽመጡ የሚገቡ ከሆነ ጥቃት እንደሚፈጽም ዝቶ ነበር።

  16. አሜሪካ ሁለት የጦር መርከቦቿ ሆርሙዝን አልፈው ፋርስ ባሕረ ሰላጤ ላይ እየተንቀሳቀሱ ገለጸች

    አሜሪካ ጦር ሚሳዔል የታጠቁ ሁለት የባሕር ኃይል አውዳሚ የጦር መርከቦቹ ኢራን እገዳ በጣለችበት ሆርሙዝ ወሽመጥ አልፈው በፋርስ ባሕረ ሰላጤ ላይ እየተንቀሳቀሱ መሆኑን አስታወቀ።

    የአሜሪካን የመካከለኛው ምሥራቅ ወታደራዊ እንቅስቃሴዎች የሚመራው ማዕከላዊ ዕዝ እንደገለጸው፤ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በሆርሙዝ ወሽመጥ መዘጋት የተነሳ ማለፊያ ያጡ የንግድ መርከቦችን “እየመሩ ለማውጣት” ላስጀመሩትን ዘመቻ እገዛ እያደረገ ነው።

    ማዕከላዊ ዕዙ፤ የአሜሪካን ሰንደቅ ዓላማ የሚያውለበልቡ ሁለት የንግድ መርከቦች “በተሳካ ሁኔታ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ማለፋቸውንም” ገልጿል። በተሳካ ሁኔታ ወሽመጡን አልፈዋል የተባሉትን መርከቦች ስም ግን አልጠቀሰም።

    ማዕከላዊ ዕዙ አክሎም “የአሜሪካ ኃይሎች የንግድ መርከቦችን ጉዞ ለመመለስ የሚደረገውን ጥረት በንቃት እያገዙ ነው” ብሏል።

    የአሜሪካ ጦር ይህንን ያለው ኢራን ወደ ሆርሙዝ ወሽመጥ ለመግባት የሞከረ የአሜሪካ አውዳሚ የጦር መርከብ ላይ ጥቃት ፈጽሜያለሁ ካለች በኋላ ነው።

    ማዕከላዊ ዕዙ ባወጣው መግለጫ ተፈጽሟል የተባለውን ጥቃት አስተባብሏል። አንድም የአሜሪካ መርከብ አልተመታም ያለው ማዕከላዊ ዕዙ፤ የአሜሪካ ኃይሎች ዘመቻውን እየደገፉ እና “በኢራን ወደቦች ላይ የተጣለን የጉዞ እገዳ እያስፈጸሙ” መሆኑን ገልጿል።

  17. ኢራን በአሜሪካ ጦር መርከብ ላይ ጥቃት ፈጸምኩ ካለች በኋላ የነዳጅ ዋጋ ጨመረ

    የኢራን መንግሥት መገናኛ ብዙኃን ወደ ሆርሙዝ ወሽመጥ ለመግባት የሞከረ የአሜሪካ የጦር መርከብ በሁለት ሚሳዔል መመታቱን ከዘገቡ በኋላ የነዳጅ ዋጋ የጎላ ጭማሪ አሳየ።

    ለዓለም የነዳጅ ንግድ የዋጋ መነሻ የሆነው ብሬንት የአንድ በርሜል የድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ ዜናው ከተሰማ በኋላ በደቂቃዎች ውስጥ ከአራት ዶላር በላይ ጭማሪ አሳይቶ 114 ዶላር ደርሷል። ይህም በዕለቱ የነዳጅ ዋጋ ላይ ከአምስት በመቶ በላይ ጭማሪን አስከትሏል።

    ኢራን በአሜሪካ የጦር መርከቦች ላይ ጥቃት መፈጸሟን ከገለጸች በኋላ ዩናይትድ ስቴትስ ማስተባበያ ያወጣች ሲሆን፣ ይህንንም ተከትሎም ዋጋው ቅናሽ አሳይቷል።

    ትናንት ምሽት ፕሬዝዳንት ትራምፕ በሆርሙዝ ወሽመጥ መተላለፊያ አጥተው የቆሙ የጭነት መርከቦችን በማጀብ ከአካባቢው የማስወጣት ዕቅዳቸውን አሳውቀው ነበር። ይህንንም ዕቅድ “ሰብአዊነት ማሳያ” ሲሉ ገልጸውታል።

    በባሕረ ሰላጤው አካባቢ የተቀሰቀሰውን ጦርነት ተከትሎ 20 በመቶ የዓለም ነዳጅ አቅርቦትን የሚያጓጉዙ በርካታ መርከቦች ከነጭነታቸው መንቀሳቀስ ሳይችሉ ባሉበት እየተጉላሉ ይገኛሉ።

    ይህ የአሜሪካ መርከቦች በባሕረ ሰላጤው በኩል እንዲያልፉ የማድረግ ዕቅድ ሌላ ዙር ግጭትን የሚቀሰቅስ ከሆነ በአሁኑ ወቅት በተወሰነ መጠን እያለፈ ያለውን የነዳጅ እና የጋዝ አቅርቦትን በማስቆም የዓለም የነዳጅ ዋጋ የበለጠ እንዲነር ያደርጋል የሚል ስጋት ፈጥሯል።

  18. የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የነበረ ነዳጅ ጫኝ መርከቧ መመታቱን አስታወቀች

    የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ‘አድኖክ’ ከተባለው የመንግሥት የነዳጅ ኩባንያ ጋር ግንኙነት ያለው ነዳጅ ጫኝ መርከቧ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ሲጓዝ ጥቃት እንደተፈጸመበት ገለጸች።

    የኤምሬቶች የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ እንዳስታወቀው በጥቃቱ የተጎዳ ሰው የለም።

    ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ “በኢራን አብዮታዊ ዘብ” ተፈጽሟል ያለውን ይህንን ጥቃት “የባሕር ውንብድና” ሲል አውግዞታል።

    የኢራን ጦር “ንግድ መርከቦችን ዒላማ ያደረገ ጥቃት እየፈጸመ እና የሆርሙዝ ወሽመጥን ለኢኮኖሚ ማስገደጃነት ወይም ለዛቻ መሣሪያነት” እየተጠቀመ ነው ሲልም ወቅሷል።

    ይህ አይነቱ ጥቃት “በቀጣናው መረጋጋት፣ በሕዝቦቹ እና በዓለም አቀፍ የኤነርጂ ደኅንነት ላይ ቀጥተኛ ስጋት የሚጋርጥ ነው" ሲልም ተቃውሟል።

    ድርጊቱ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት ውሳኔን “በግልጽ የጣሰ” እንደሆነ የገለጸችው የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች፤ ኢራን ጥቃት መፈጸም እንድታቆም ጠይቃለች።

    "ሁሉንም ጠበኛ ድርጊቶች በአስቸኳይ ለማቆም እንዲሁም የሆርሙዝ ወሽመጥን ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ሙሉ በሙሉ ለመክፈት ያላትን ቁርጠኝነት እንድታረጋግጥም" ጥሪ አቅርባለች።

  19. ኢራን ወደ ሆርሙዝ ወሽመጥ ሊገባ የነበረን የአሜሪካ የጦር መርከብን በሚሳዔል መምታቷን ገለጸች

    የኢራን ጦር ወደ ሆርሙዝ ሊገባ የነበረ የአሜሪካ ባሕር ኃይል አውዳሚ የጦር መርከብን በሁለት ሚሳዔል በመምታት ወደ ወሽመጡ እንዳይገባ መከልከሉን ገለጸ።

    የኢራን መንግሥት መገናኛ ብዙኃን የአገሪቱን ጦር የሕዝብ ግንኙነት ጠቅሰው ባወጡት ዘገባ፤ "ከእስላማዊ ሪፐብሊክ ባሕር ኃይል በተሰጠው ጠንካራ እና ፈጣን ትዕዛዝ የአሜሪካ እና የጽዮናዊው ጠላት አውዳሚ መርከቦች ወደ ሆርሙዝ ወሽመጥ እንዳይገቡ ተከልክለዋል" ብለዋል።

    ከፊል ይፋዊ የዜና ወኪል የሆነው ፋርስ፤ የኢራን ባሕር ኃይል ጦር ሠፈር መገኛ በሆነው ጃስክ ወደብ አቅራቢያ አንድ የጦር መርከብ በሁለት ሚሳዔሎች መመታቱን ዘግቧል።

    የጦር መርከቡ በወሽመጡ ደቡባዊ መግቢያ በኩል ሲቀዝፍ የነበረው “የባሕር ላይ ትራፊክ እና የመርከብ ጉዞ ደኅነትን በመጣስ” እንደሆነ ዘገባው ጠቅሷል።

    እንደ ፋርስ ዘገባ ከሆነ የአሜሪካው የጦር መርከብ “ለማፈግፈግ እና ከአካባቢው ለመሸሽ ተገድዷል።”

    አክሲዮስ የተሰኘው የዜና ምንጭ ጋዜጠኛ ያነገጋራቸው አንድ የአሜሪካ ባለሥልጣን ግን የጦር መርከቡ በኢራን ሚሳዔሎች ተመትቷል መባሉን አስተባብለዋል።

    የኢራን ጦር ይህንን ያለው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የአሜሪካ ጦር በወሳኙ የባሕር ወሽመጥ ላይ ማለፊያ አጥተው የቆዩ መርከቦች ጉዟቸውን እንዲቀጥሉ እገዛ እንደሚያደርግ ከተናገሩ ከሰዓታት በኋላ ነው።

    “ፕሮጀክት ፍሪደም” በተባለው በዚህ ዘመቻ ላይ 15 ሺህ ወታደሮች፣ ሚሳዔል ተሸካሚ አውዳሚ መርከቦች እና ከ100 በላይ ተዋጊ አውሮፕላኖች እንደሚሳተፉም ተገልጿል።

    ይህንን ተከትሎም ኢራን "ለአሜሪካ ዛቻዎች ምላሽ ለመስጠት" ዝግጁ መሆኗን ተናግራለች።

  20. የዩኬ ባሕር ትራንስፖርት ባለሥልጣናት በሆርሙዝ ወሽመጥ አደገኛ ስጋት መኖሩን አስጠነቀቁ

    የሆርሙዝ ወሽመጥን ለማቋረጥ የሚሞክሩ መርከቦች “በቀጣናው እየተካሄዱ በሚገኙ ወታደራዊ ዘመቻዎች” ምከንያት “አደገኛ የደህንነት ስጋት” እንደሚገጥማቸው የዩኬ የባሕር ትራንስፖርት እና ንግድ ሥራዎች ማዕከል አስጠነቀቀ።

    የባሕር ትራንስፖርት ባለሥልጣኑ መርከቦች “የፈንጂዎችን አደጋ ወይም ለመጓዝ ባሰቡበት መስመር የሚኖር ሌላ የአደጋ ስጋትን” ከግምት ውስጥ ሊያስገቡ እንደሚገባ ተናግረዋል።

    በወሽመጡ ውስጥ ማለፍ ወይም በጉዞ መለያ ስፍራው መጓዝ በጣም አደገኛ መሆኑን ባለሥልጣኑ ጨምሮ ገልጿል።

    ምክንያቱም ያልተገኙ እና እንዲወገዱ ያልተደረጉ ፈንጂዎች ሊኖሩ እንደሚችሉ ወይም ደህንነቱ ያልተጠበቀ መስመር ሊሆን እደሚችል አስጠንቅቋል።

    የጉዞ መለያ መስመር ማለት በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚያልፉ መርከቦችን በሚመለከት እአአ በ1968 የተደረሰ ዓለም አቀፍ ስምምነት ነው።